የዩክሬንን እህል የጫነች የመጀመሪያዋ መርከብ ከኦዴሳ ወደብ ተነሥታ ወደ ሊባኖስ ማምራቷን የቱርክ መከላከያ ሚኒስቴር ገለጸ። ዩክሬን የእህል ምርቶቿን ወደ ሌሎች ሀገራት መላክ የሚያስችላትን ስምምነት ከሩሲያ ጋር መፈራረሟ የሚታወስ ነው። ስምምነቱን ያሳለጡት ደግሞ ቱርክ እና የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ናቸው። በዚሁ ስምምነት መሠረት በሩሲያ እና በዩክሬን መካከል ጦርነት ከተጀመረ ከ6 ወራት በኋላ እህል የጫነች የመጀመሪያዋ መርከብ ከኦዴሳ ወደብ ተነሥታ ወደ ሊባኖስ ማምራቷን ቲአርቲ የቱርክ መከላከያ ሚኒስቴርን ጠቅሶ ዘግቧል። እንደ አልጀዚራ ዘገባ ደግሞ ራዞኒ የተባለች የሴራሊዮን ዕቃ ጫኝ መርከብ ከ26 ሺህ ቶን በላይ በቆሎ ጭና ከኦዴሳ ወደብ ወደ ሊባኖስ አምርታለች።