ኢትዮጵያ የፕሪቶሪያው የሰላም ስምምነት ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ እንዲሆን ጥረቷን በእጥፍ አጠናክራ ትቀጥላለች

1 Yr Ago
ኢትዮጵያ የፕሪቶሪያው የሰላም ስምምነት ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ እንዲሆን ጥረቷን በእጥፍ አጠናክራ ትቀጥላለች

ኢትዮጵያ የፕሪቶሪያው የሰላም ስምምነት ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ እንዲሆን ጥረቷን በእጥፍ አጠናክራ እንደምትቀጥል ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አቶ ደመቀ መኮንን አረጋገጡ።

አቶ ደመቀ ይህን ያረጋገጡት ዛሬ በተጀመረው የአፍሪካ ኅብረት የሥራ አስፈጻሚዎች ምክር ቤት 42ኛ መደበኛ ጉባኤ ማስጀመሪያ ሥነ-ሥርዓት ላይ ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር ነው።

ጉባኤው የተጀመረው ኢትዮጵያ በደቡብ አፍሪካ፣ ፕሪቶሪያ የተፈረመውን የሰላም ስምምንት ተግባራዊ በማድረጉ ሂደት እመርታዎችን እያሳያች ባለበት ወቅት በመሆኑ ለኢትዮጵያ ትልቅ ፋይዳ እንዳለው ገልጸዋል። 

ኢትዮጵያ አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ በነበረችበት አጋጣሚ በብዙ መድረኮች ከጎኗ በመቆም አጋርነታቸውን ላሳዩ አፍሪካዊያንም ምስጋናቸወን አቅርበዋል።

የአፍሪካ አገራት እና የአፍሪካ ኅብረት እንዲሁም አጋር አካላት በኢትዮጵያ በዘላቂነት ግጭት ለማቆም ለተደረሰው ሥምምነት ላደረጉት ድጋፍ ምስጋና አቅርበዋል።

በተለይም ደግሞ አንዳንድ አካላት በኢትዮጵያ ላይ ጫና ሲያሳድሩ በባለብዙ ወገን መድረኮችም ላይ ጭምር አፍሪካዊያን ከኢትዮጵያ ጋር በመሰለፍ አጋርነታቸውን ማሳየታቸውን አስታውሰዋል። 

ኢትዮጵያ ባሳለፈቻቸው የፈተና ጊዜያት ከአፍሪካ ኅብረት እና ከአፍሪካዊያን ያገኘነው ድጋፍ አኩርቶናል፣ በአፍሪካ ላይ ያለንን እምነትም እጅጉን አጠናክሮታል ብለዋል።

በተለይም ለአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ሊቀ-መንበር ሙሳ ፋቂ ማህመት፣ ለቀድሞ የናይጄሪያ ፕሬዚዳንት ኦሊሴጉን ኦባሳንጆ እንዲሁም ለቀድሞ ኬንያ ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬንያታ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።

በመንግሥት እና በሕወሓተ መካከል የተደረሰው የሠላም ሥምምነት "አፍሪካዊ ችግሮች የአፍሪካዊ መፍትሔ መስጠት" የሚለውን የኅብረቱ ቁልፍ መርሕ ገቢራዊ በማድረግ ትልቅ መሳያ ነው ሲሉም ተናግረዋል።


አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ

ግብረመልስ
Top