ኢትዮጵያና ናሚቢያ በሰላምና ደህንነት ጉዳዮች ላይ በጋራ ለመስራት ተስማሙ

1 Yr Ago
ኢትዮጵያና ናሚቢያ በሰላምና ደህንነት ጉዳዮች ላይ በጋራ ለመስራት ተስማሙ

ኢትዮጵያ እና ናሚቢያ በሰላምና ደህንነት ጉዳዮች ዙሪያ በጋራ ለመስራት የሚያስችላቸውን ስምምነት ተፈራረሙ።

ስምምነቱን የኢፌዴሪ መከላከያ ሚኒስትር ዶክተር አብርሃም በላይ እና የናሚቢያ ምክትል ጠቅላይ ማኒስትርና የዓለም አቀፍ ግንኙነትና ትብብር ሚኒስትር ኔቱምቦ ናንዲ ንዳይትዋህ ተፈራርመዋል።

የናሚቢያ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የዓለም አቀፍ ግንኙነትና ትብብር ሚኒስትር ኔቱምቦ ናንዲ ንዳይትዋህ በስምምነቱ ወቅት እንዳሉት የሁለቱ ሀገራት ትብብር ከናሚቢያ ከቅኝ ግዛት ነጻ መውጣት ጋር በጥብቅ የተቆራኘ ነው።

ናሚቢያ ከቅኝ ገዥዎች ነፃ በወጣችበት ወቅት የኢትዮጵያ ተሳትፎ የጎላ እንደነበር ገልጸዋል።

ሀገራቱ በዘርፉ በስልጠና፣ በአየር ትራንስፖርት፣ በኢኮኖሚ እንዲሁም በባህል መስኮች በጋራ ለመስራት መስማማታቸውን ገልጸዋል።

ስምምነቱ በኢትዮጵያ እና በናሚቢያ መካከል ጠንካራ ትብብር ለመፍጠር መሰረት የሚጥል መሆኑንም አክለዋል።

የሰላምና ጸጥታ ጉዳይ ዓለም አቀፍ ይዘት ያለው በመሆኑ በቀጣናው ውጤታማ ስራዎችን በጋራ ለማከናወን ያስችላል ብለዋል።

የመከላከያ ሚኒስትር ዶክተር አብርሃም በላይ በበኩላቸው ሁለቱ ሀገራት የቆየ የዲፕሎማሲ ትስስር አላቸው ብለዋል።

በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን የመከላከያና የጸጥታ ግንኙነት ይበልጥ ለማጠናከር ያለመ ስምምነት ተፈራርመናል ነው ያሉት።

ሁለቱ ወገኖች በአየር ሀይል፣ በባህር ሀይልና በሌሎችም ዘርፎች የአቅም ግንባታ ወታደራዊ ስልጠናዎችን በጋራ ለማከናወን የሚያስችል የመግባቢያ ሰነድ መፈራረማቸውን ኢዜአ ዘግቧል።


ተያያዥ ርዕሶች

አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ

ግብረመልስ
Top