የቅዱስ ጊዮርጊስ እግር ኳስ ክለብ የዋናው ቡድን ዋና አሠልጣኝ የነበረውን ዘሪሁን ሸንገታን እና የበረኞች አሠልጣኝ ውብሸት ደሳለኝን ከማሰልጠን ተግባራቸው ማገዱን አስታውቋል።
የክለቡ ስፖርት ማህበር ስራ አመራር ቦርድ ዛሬ ባደረገው አስቸኳይ ስብሰባ የዋናውን ቡድን እንቅስቃሴ ከገመገመ በኋላ ተለዋጭ መመሪያ እስኪሰጥ ድረስ ይህን ውሳኔ ማሳለፉን ገልጿል፡፡
በምትኩም የዋናው ቡድን ምክትል አሠልጣኝ የነበረው ደረጀ ተስፋዬ ዋና አሠልጣኝ ሆኖ ከሚያዝያ 29 ቀን 2016 ዓ.ም ጀምሮ በጊዜያዊነት እንዲያሠለጥን መወሰኑን ከክለቡ የማህበራዊ ትስስር ገፅ የተገኘው መረጃ አመላክቷል፡፡
እንዲሁም የክለቡ የወጣት ቡድን ዋና አሠልጣኝ የነበረው አሠልጣኝ ሳምሶን ሙሉጌታ የዋናው ቡድን ምክትል አሠልጣኝ ሆኖ በጊዜያዊነት እንዲያሠለጥን መወሰኑ ተጠቁሟል፡፡