በፅንፈኛው አመራርና አባላት ላይ በአዲስ አበባ እርምጃ ተወሰደ ፡- ፖሊስ

17 Days Ago
በፅንፈኛው አመራርና አባላት ላይ በአዲስ አበባ እርምጃ ተወሰደ ፡- ፖሊስ
በፅንፈኛው አመራርና አባላት ላይ በአዲስ አበባ እርምጃ ተወሰደ ፡- ፖሊስ
 
በኦሮሚያ ክልል አንዳንድ አካባቢዎች ላይ የሚንቀሳቀሰው የሸኔ የሽብር ቡድን ላይ እና በፅንፈኛ የታጣቂ ቡድን ላይ የማያዳግም እርምጃ እየተወሰደ ነው ፡- ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ ጁላ
****************
 
የአዲስ አበባ ፖሊስ አንዳስታወቀው በፅንፈኛው አመራርና አባላት ላይ በአዲስ አበባ እርምጃ ተወስዷል፡፡ የፅንፈኛው አመራርና አንድ የቡድኑ አባል ሲገደሉ አንደኛው በቁጥጥር ስር ውሏልም ብሏል፡፡
 
የፅንፈኛው ቡድን አባላት የሆኑት ናሁሰናይ አንድአርጌ ታረቀኝ ፣ አቤኔዜር ጋሻው አባተ እና ሀብታሙ አንድአርጌ ተሰማ የተባሉት የቡድኑ አባላት በአዲስ አበባ የሽብር ጥቃት ለመፈፀም ተልዕኮ ይዘው እየተንቃሰቀሱ መሆኑን የፀጥታ አካላት ባደረጉት ክትትል ተደርሶበታል፡፡
 
አሸባሪዎቹ የሽብር ተግባራቸውን ሳይፈፅሙ በቁጥጥር ስር ለማዋል የፖሊስ አባላት እንቅስቃሴ እያደረጉ ባለበት ሁኔታ፤ ሚያዚያ 4 ቀን 2016 ዓ/ም ቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 3 ልዩ ቦታው ሚሊኒዬም አዳራሽ አካባቢ ፅንፈኞቹ እጃቸውን እንዲሰጡ ቢጠየቁም ፍቃደኛ ባለመሆን በሰሌዳ ቁጥር ኮድ 2C 14373 አ/አ አይነቷ ሱዙኪ ዲዛዬር መኪናን በመጠቀም ከፖሊስ አባላት ጋር ተኩስ በመክፈታቸው የፅንፈኛው መሪ ናሁሰናይ አንዳርጌ ታረቀኝ ቆስሎ ወደ ህክምና ከተላከ በኋላ ሲሞት፤ ፅንፈኛው ሀብታሙ አንዳርጌ ተሰማ በተኩስ ልውውጡ መሃል ተገድሏል፡፡
 
አቤኔዘር ጋሻው አባት የተባለው የቡድኑ አባል ሳይቆስል በቁጥጥር ስር መዋሉን አዲስ አበባ ፖሊስ አስታውቋል፡፡
 
ፅንፈኞቹን በቁጥጥር ስር ለማዋል በተደረገ እንቅስቃሴ ሳጅን አራርሳ ተሾመ እና ኮንስታብል ማቲያስ ጴጥሮስ ቆስለዋል፡፡
 
አቶ እንዳሻው ጌትነት የተባሉ ግለሰብ ፅንፈኞቹ በመኪናቸው እንዲጭኗቸው ቢያስገድዷቸውም ግለሰቡ አልተባበርም በማለታቸው በፅንፈኛው አባላት ተገድለዋል፡፡
 
አቶ እንደሻው ሲያሽከርክሯት የነበረቸው የሰሌዳ ቁጥር ኮድ 2 አ/አ 80457 በጥይት ጉዳት እንደረሰባት አዲስ አበባ ፖሊስ ጨምሮ ገልጿል ፡፡ በቀጣይ ፖሊስ የደረሰበትን ዝርዝር መረጃ እንደሚገልፅ አስታውቋል፡፡
 
ከዚህ ቀደም በአዲስ አበባ እና አዋሳኝ አካባቢዎች በትጥቅ የታገዘ ሁከት እና ብጥብጥ ለመፈፀም በህቡዕ ሲንቀሳቀሱ የነበሩ 50 ተጠርጠሪዎች በጸጥታና ደኅንነት የጋራ ግብረ- ኃይል በቁጥጥር ስር መዋላቸውም ይታወሳል፡፡
 
ከዚህ ጋር በተያያዘም በኦሮሚያ ክልል አንዳንድ አካባቢዎች ላይ የሚንቀሳቀሰው የሸኔ የሽብር ቡድን ላይ እና በፅንፈኛ የታጣቂ ቡድን ላይ የማያዳግም እርምጃ እየተወሰደ መሆኑን ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ ጁላ ለኢቢሲ ገልፀዋል፡፡
 
ፊልድ ማርሻሉ የሀገር መከላከያ ሠራዊት ታጣቂ ቡድኖቹን በሚገባ እየደመሰሰ መሆኑና ታጣቂ ኃይሎቹ ከጦር ሜዳ ወጥተው የሚዲያ ፕሮፖጋንዳ ላይ እንዲሰሩ እያደረጋቸው መሆኑን ከኢቢሲ ጋር በነበራቸው ቆይታ አረጋግጠዋል፡፡

አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ

ግብረመልስ
Top