ኢትዮጵያ በቻይና የግሎባል ፐብሊክ ሴኩሪቲ ትብብር ፎረም ዳይሬክተሮች ቦርድ ስብሰባ ላይ እየተሳተፈች ነው

18 Days Ago
ኢትዮጵያ በቻይና የግሎባል ፐብሊክ ሴኩሪቲ ትብብር ፎረም ዳይሬክተሮች ቦርድ ስብሰባ ላይ እየተሳተፈች ነው
ኢትዮጵያ በቻይና ናንቶንግ ከተማ እየተካሄደ በሚገኘው የግሎባል ፐብሊክ ሴኩሪቲ ትብብር ፎረም ዳይሬክተሮች ቦርድ ስብሰባ ላይ እየተሳተፈች ትገኛለች።
 
የግሎባል ፐብሊክ ሴኩሪቲ ትብብር ፎረም የዳይሬክተሮች ቦርድ አባል የሆኑት የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ ገ/ሚካኤል ፤ ከሚያዚያ 1 እስከ 3/2016 ዓ.ም. እየተካሄደ ባለው ስብሰባ ላይ እየተሳተፉ ይገኛሉ፡፡
 
መድኩ የፎረሙ ዓመታዊ የስራ ክንውን ሪፖርት በተመለከተ ፣ የግሎባል ሴኩሪቲ ኢንዴክስ ላይ ስለሚደረገው ጥናት ሂደት እና የፎረሙ የ2024 ዓመታዊ ኮንፈረስ ዝግጅትን አስመልክቶ ውይይት በማድረግ የተለያየ ውሳኔዎችን ያሳልፋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
 
የትብብር ፎረሙ ኢትዮጵያን ጨምሮ ከዘጠኝ ሀገራት የተውጣጡ ከፍተኛ የቦርድ ዳይሬክተሮች የሚመራ ሲሆን ፤ በዓለም ዓቀፍ ደረጃ የህዝብ ደኅንነት ላይ በማተኮር የሀገሮችን የሕግ አስከባሪ ተቋማትን በማስተባበር ልዩ ልዩ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል፡፡
 
ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ ከቦርድ አመራር ጉባኤው ጎን ለጎን በቻይና የሚገኙ ልዩ ልዩ ተቋማትን መጎብኘታቸው ተገልጿል፡፡
 
በዚህም በጃንሱ ግዛት የሚገኘው ሞተር ሳይክል አምራች የሆነውን ሲ ኤፍ ሞተር መጎብኘታቸው የተጠቀሰ ሲሆን፤ ካምፓኒው በኢትዮጵያ ቅርንጫፉን በመክፈት ለመስራት ፍላጎት እንዳለውም መግለጹ ተጠቁሟል፡፡
 
ኮሚሽነር ጀነራሉ በተጨማሪም የቺንጃን ፖሊስ ኮሌጅን የጎበኙ ሲሆን ፤ በአሁኑ ወቅት በኮሌጁ ነጻ የትምህርት እድል አግኝተው እየሰለጠኑ ላሉት የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ አባላት ኮሌጁ ለሰጠው ነፃ የትምህርት ዕድል አመሥግነዋል፡፡
 
በኢትዮጵያ ፖሊስ ዩንቨርሰቲ የኢንተርናሽናል ፖሊስ ሊደርሺፕ ኢንስቲቱት ለማቋቋም እየተሰራ መሆኑን የጠቀሱት ኮሚሽነር ጀነራሉ፤ ኮሌጁ ከዩንቨርስቲው ጋር በትብብር እንዲሰራ መጠየቃቸውን ከፌዴራል ፖሊስ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።

አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ

ግብረመልስ
Top