Search

በካንሰርም በፈረንሳይ ግብአዳኞችም የተፈተነችው ግብ ጠባቂ

አን ካትሪን በርገር ትባላለች ጀርመናዊት ግብ ጠባቂ ናት፡፡ በአውሮፓ ታላላቅ ክለቦች በፒኤስጂ፣ ቼልሲ እና በርሚንግሀም ለመሳሰሉ ክለቦች ተጫውታለች፡፡ ሀገሯንም 2020 ጀምሮ በታላ መድረኮች ወክላለች።

ሕይወት 2 ዕድል ከሰጠቻቸው ሰዎች አንዷናት፡፡ አስቸጋሪ የሚባለው የካንሰር ህመም ከአንድም ሁለት ጊዜ  ያቀረበላትን ፈተና በድል ተወጥታለች፡፡

አን ካትሪን በርገር 2017 የበርሚንግ ተጫዋች በነበረችበት ጊዜ ነው  ለመጀመርያ  ጊዜ የታይሮይድ ካንሰር ህምም እንዳጋጠማት በህክምና ያረጋገጠችው፡፡

በዚሁ ምክንያት ከእግር ኳስ የተገለለችው  ግብ ጠባቂዋ 4 ወራት ባደረገችው ህክምና ከባድ የሚባለውን ህመም አሸንፋ ዳግም ወደ ሜዳ ተመለሰች፡፡ የበርሚንግ ውሏን ስታጠናቅቅ 2019 ወደ ቼልሲ የተዛወረችው በርገር በምራብ ለንደኑ ክለብ እያለች 2022 የአውሮፓ ዋንጫ በጀርመን ብሔራዊ ቡድን ጥሪ ደረሳት፡፡

በእንግሊዝ አስተናጋጅነት በተካሄደው የአውሮፓ ዋንጫ በርገር የስብስቡ አካል ብትሆንም በበርሚንግሀም እያለች ገጥሟት የነበረው የካንሰር ህመም እንደገና ተመለሰባት፡፡

በመድረኩ አንድም ጨዋታ ማድረግ ያልቻለችው ግብ ጠባቂ  ለሁለተኛ ጊዜ የገጠማትን ካንሰር በብዙ የህክምና ክትትል እና የአካል ብቃት እንቅስቃሴ አሸንፋ ወደ እግር ኳስ ሜዳ ተመልሳለች፡፡

አን ካትሪን በርገር አስቸጋሪውን የካንሰር ፈተና ከተወጣች በኋላ ከቼልሲ ጋር አራት  የሱፐር ሊግ ዋንጫዎችን ጨምሮ በአጠቃላይ 10 ክብሮችን በማሸነፍ የተሳኩ አመታትን አሳልፋለች፡፡

ከዚህ ሁሉ ፈተና ያመለጠችው በርገር በሲውዘርላንድ አስተናጋጅነት እየተካሄደ በሚገኘው የሴቶች አውሮፓ ዋንጫ የጀርመን ብሔራዊ ቡድን ቁጥር አንድ ግብ ጠባቂ ሆና እያገለገለች ትገኛል፡፡

34 አመቷ ላይ የምትገኘው ካትሪን በርገር ጀርመን በሩብ ፍጻሜው ፈረንሳይን በመለያ ምት አሸንፋ ለግማሽ ፍጻሜ ስትደረስ ትልቁን የቤት ስራ በብቃት ተወጥታለች፡፡ ገና 13ኛው ደቂቃ አንድ ተጫዋቿን በቀይ ካርድ ያጣችው ጀርመን 75 ደቂቃ በላይ በፈረንሳይ ብትፈተንም ለፈተና አዲስ ባልሆነችው ግብ ጠባቂ የግል ጥረት ግማሽ ፍጻሜውን ተቀላቅላለች፡፡

እንደ  አቦሸማኔ   የምትወረወረው ካትሪን በርገር በጨዋታው 9 ግብ መሆን የሚችሉ ሙከራዎችን እና ሁለት የመለያ ምቶችን አድናለች፡፡

በካንሰርም በፈረንሳይ ግብ አዳኞችም የተፈተነችው በርገር በአውሮፓ ዋንጫ ታሪክ በጥሎ ማለፍ ጨዋታ ያዳነቻቸው ኳሶች ብዛት 2013 በኋላ 2ኛው ትልቅ ቁጥር ሆኖም ተመዝግቧል፡፡

ሀገሯን ለግማሽ ፍጻሜ ያበቃችወ 34 አመቷ ግብ ጠባቂ ዛሬ ምሽት 4 ሰዓት ላይ ጀርመን ለፍጻሜ ለማለፍ ከስፔን በምታደርገው ጨዋታ ለሌላ ታሪክ ተዘጋጅታለች።

 

 

በአንተነህ ሲሳይ