የጉምሩክ ኮሚሽን ከጥቅምት 29 እስከ ህዳር 5 ቀን 2016 ዓ.ም ባደረገው ክትትል፥ የ224 ነጥብ 7 ሚሊዮን ብር የገቢ እና የ59 ነጥብ 7 ሚሊዮን ብር የወጭ፤ በድምሩ 284 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር የሚያወጡ የኮንትሮባንድ እቃዎች በተለያዩ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤቶች ተይዘዋል።
በቁጥጥር ስር ከዋሉት የኮንትሮባንድ እቃዎች መካከል አልባሳት፣ ነዳጅ፣ የቁም እንስሳት፣ ኤሌክትሮኒክስ፣ ቡና፣ መድሀኒት፣ ተሽከርካሪዎች፣ የመዋቢያ እቃዎች የጦር መሳሪያዎች፣ ጫት፣ አደንዛዥ እጾች፣ የምግብ ዘይት እና የተለያዩ ሀገራት ገንዘቦች ይገኙበታል።
የኮንትሮባንድ እቃዎቹ የጉምሩክ ኮሚሽን ሰራተኞች፣ የፌደራልና የክልል ፖሊስ አባላትና ህብረተሰቡ ባደረጉት የጋራ ጥረት በፍተሻ፣ በበረራና በጥቆማ የተያዙ ሲሆን፤ ኮንትሮባንዱን ሲያዘዋውሩ የተገኙ 29 ተጠርጣሪዎች እና 9 ተሽከርካሪዎችም በቁጥጥር ስር ውለዋል።
የጉምሩክ ኮሚሽን በሕግ ማስከበር ስራው ለተሳተፉ የኮሚሽኑ ሰራተኞች፣ የክልልና የፌደራል ፖሊስ አባላት እንዲሁም ህብረተሰቡን አመስግኖ ወደፊትም ጥረታቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ ጥሪ አቅርቧል።