መከላከያ ሰራዊትን በእውቀትና በቴክኖሎጂ የመገንባቱ ስራ ተጠናክሮ ይቀጥላል - ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ

17 Days Ago
መከላከያ ሰራዊትን በእውቀትና በቴክኖሎጂ የመገንባቱ ስራ ተጠናክሮ ይቀጥላል - ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ

መከላከያ ሰራዊቱን በአደረጃጀት፣ በእውቀትና በቴክኖሎጂ የመገንባቱ ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የጦር ሃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ገለጹ።

ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ለቤላ ኮምፕሬሄንሲቭ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ግንባታ የመሠረተ ድንጋይ አስቀምጠዋል።

በዚሁ ወቅት ባደረጉት ንግግር፤ በሁሉም ዘርፎች ኢትዮጵያን የሚመጥን ሰራዊት የመገንባት ሂደቱ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።

ሰራዊቱን በአደረጃጀት፣ በእውቀት፣ በቴክኖሎጂ እንዲሁም በሁሉም ዘርፎች የመገንባት ሂደቱ ተጠናክሮ መቀጠሉን ጠቁመው፤ ሰራዊቱ በሁሉም ዘርፎች ፕሮፌሽናል ሆኖ እንዲገኝ ይሰራልም ነው ያሉት።

የሠራዊቱን ዕድገት የሚመጥን የመሠረተ ልማት ግንባታ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ጠቁመው፤ በዛሬው ዕለት የግንባታው ሂደት የተጀመረው ሆስፒታልም የዚሁ ማሳያ ነው ማለታቸውን ኢዜአ ዘግቧል።

ብቃትና ጥራት ያለው የጤና አገልግሎት የዘመናዊ ሠራዊት ግንባታ መሠረት መሆኑንም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ተናግረዋል፡፡

የመሠረተ ልማቶች መስፋፋት የሠራቱን ግንባታ ከማሳለጥ አንጻር ሚናቸው የጎላ መሆኑንም አብራርተዋል፡፡

የቤላ ኮምፕርሄንሲቭ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ግንባታ ከተጠናቀቀ በኋላ የጦር ሃይሎች ሆስፒታልን ዓለም አቀፍ ደረጃውን በጠበቀ መልኩ የመገንባት ሂደት እንደሚጀመርም ጠቁመዋል።

የመከላከያ ሠራዊት ጤና ዋና መምሪያ ኃላፊ ሌተናል ጀነራል ጥጋቡ ይልማ፤ የሆስፒታል ግንባታው በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ እንደሚጠናቀቅ ተናግረዋል፡፡

ግንባታው የህክምና አገልግሎት የሚሰጡ ህንጻዎች፣ የመማሪያ ክፍሎች እና ሌሎች አገልግሎት መስጫ ማዕከላትን ያካተተ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡


አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ

ግብረመልስ
Top