የሚኒስትሮች ም/ቤት በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ አሳለፈ

1 Yr Ago
የሚኒስትሮች ም/ቤት በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ አሳለፈ
የሚኒስትሮች ም/ቤት በዛሬው ዕለት ባካሄደው 10ኛ መደበኛ ስብሰባ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ አሳለፈ፤ ውሳኔዎቹም የሚከተሉት ናቸው፥
1. ምክር ቤቱ በቀዳሚነት የተወያየው የነዳጅና ኢነርጂ ባለስልጣንን አደረጃጀት፣ ስልጣንና ተግባራትን ለመወሰን በቀረበው ደንብ ላይ ሲሆን የፌዴራል መንግስት የአስፈላሚ አካላትን ሥልጣንና ተግባር ለመወሰን የወጣው አዋጅ ቁጥር 3263/2014 የነዳጅና ኢነርጂ ጉዳዮችን የሚመራ ተቋም በአዲስ መልክ ያቋቋመ መሆኑን ተከትሎ ባለስልጣኑ ሴክተሩን በብቃት መምራት የሚያስችል ስልጣንና ተግባር እንዲኖረው የሚያስቸል ደንብ ተዘጋጅቶ ለሚኒስትሮች ምክር ቤት ቀርቧል። ምክር ቤቱም በደንቡ ላይ በሰፊው ከተወያየ በኋላ ግብዓቶችን በማከል በነጋሪት ጋዜጣ ታትሞ ከወጣበት ቀን ጀምሮ በስራ ላይ እንዲወል ወስኗል።
2. በመቀጠል ምከር ቤቱ ውይይቱን ያደረገው የብሔራዊ የክፍያ ስርዓት አዋጅን ለማሻሻል በቀረበው ረቂቅ አዋጅ ላይ ነው። ቀደም ሲል የነበረውን አዋጅ ማሻሻል ያስፈለገበት ዋነኛ ምክንያት አገራችን በጀመረቸው አጠቃላይ አገራዊ የሪፎርም አጀንዳ ማዕቀፍ ውስጥ የክፍያ አገልግሎት ሰጪዎችን ተሳትፎ በማስፋት የክፍያ ስርአቱን ውጤታማነት፣ አስተማማኝነትና ተወዳዳሪነት ለማጎልበት፣ ገበያው አበክሮ የሚፈልጋቸውንና በዘርፉ በዓለም አቀፍ ደረጃ የተደረጉትን ለውጦች፣ ዕድገቶችና መሻሻሎች ታሳቢ ባደረገ መልኩ የክፍያ ስርዓታችንን ማዘመን ይቻል ዘንድ የማሻሻያ አዋጅ ተዘጋጅቶ ለምክር ቤቱ ቀርቧል። ምክር ቤቱም በረቂቅ አዋጁ ላይ ከተወያየ በኋላ ግብዓቶችን በማከል ይፀድቅ ዘንድ ወደ ህዘብ ተወካዮች ምክር ቤት እንዲተላለፍ በሙሉ ድምፅ ወስኗል።
3. ምክር ቤቱ በመቀጠል የተወያየው ከጣሊያን ሪፐብሊክ መንግስት ለጤናው ዘርፍ ዘላቂ የልማት ግቦች ፕሮጀክት እንዲሁም ከዓለዎ አቀፉ የልማት ማህበር የምግብ ስርዓት ማጠናከሪያ ፕሮግራም ማስፈፀሚያ በተፈቀዱ ብድሮች ማፅደቂያ ረቂቅ አዋጆች ላይ ነው። ከጣሊያን መንግሥት የተገኘው ብድር 10 ሚሊዮን ዩሮ ሲሆን ከዓለም አቀፉ የልማት ማህበር የተገኘው ብድር ደግሞ 46ዐ ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር ነው። ምክር ቤቱም ብድሮቹ ከ1 ፐርሰንት ያነሰ ወለድ የሚከፈልባቸው፥ እስከ 12 ዓመታት የሚደርስ የችሮታ ጊዜ ያላቸው እና በ38 ዓመታት ተከፍለው የሚጠናቀቁ መሆናቸውን ይህም ከአገራችን የብድር ፖሊሲ ጋር የሚጣጣም መሆኑን በማረጋገጥ ይፀድቁ ዘንድ ረቂቅ አዋጆቹ ወደ ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንዲተላለፉ ወስኗል።
4. ቀጥሎ ምክር ቤቱ ውይይቱን ያደረገው የፌዴራል የገቢ ግብር ደንብን ለማሻሻል በቀረበው ረቂቅ ደንብ ላይ ሲሆን በካፒታል አጥረት ምክንያት የስራ እንቅስቃሴያቸው የተዳከሙ ድርጅቶች ተጨማሪ ካፒታል ለማሰባሰብ ከሚሸጡት አዲስ አክሲዮን የሚገኝ ገቢን ከግብር ነፃ ማድረግ የሚኖረውን ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ከግምት ውስጥ በማስገባት እንደዚሁም በገቢ ግብር አዋጅ ቁጥር ቁጥር 979/2008 አንቀፅ 65 (2) ኢኮኖሚያዊ፣ አስተዳደራዊ ወይም ማህበራዊ ምክንያቶች መኖራቸው ሲታመን የሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ በማውጣት አንድን ገቢ ከግብር ነፃ ሊያደርግ እንደሚችል በተደነገገው መሰረት ረቅቅ ደንብ ተዘጋጅቶ ቀርቧል። ምክር ቤቱም በደንቡ ላይ ከተወያየ በኋላ ግብዓቶችን በማከል በነጋሪት ጋዜጣ ላይ ታትሞ ከወጣበት ቀን ጀምሮ በስራ ላይ እንዲውል ወስኗል።
5. ሌላው ምክር ቤቱ የተወያየበት አጀንዳ ወደ አገር በሚገቡ እቃዎች ላይ የማህበራዊ ልማት ቀረጥ ለማስከፈል የቀረበ ረቂቅ ደንብ ነው። ወደ አገር በሚገቡ በተወሰኑ ምርቶች ላይ አነስተኛ ቀረጥ በመጣል በሚገኘው ገቢ የማህበራዊ አገልግሎት መስጫ ተቋማትን በማስፋፋት፣ በመጠገን እና በማሻሻል የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የሚያስችል ረቂቅ ደንብ ተዘጋጅቶ ለምክር ቤቱ ቀርቧል። ምክር ቤቱም በደንቡ ላይ ከተወያየ በኋላ ግብዓቶችን በማከል በነጋሪት ጋዜጣ ላይ ታትሞ ከወጣበት ቀን ጀምሮ በስራ ላይ እንዲውል ወስኗል።
6. በመጨረሻ ምክር ቤቱ የመንግስትና የግል አጋርነት አዋጅን ለማሻሻል በቀረበው ረቂቅ አዋጅ ላይ የተወያየ ሲሆን የመንግስትና የግል አጋርነት አሰራር በዋናነት የግል ሴከተሩን እውቀት፣ ክህሎትና የፋይናንስ አቅም በመጠቀም የህዝብ አገልግሎት መስጫ መሰረተ ልማቶችን ጥራትና ደረጃ ለማሳደግና ለማስፋፋት፣ ስራው በግልፅ ውድድርና ፍትሃዊነት እንዲፈፀም ለማድረግ እንዲሁም በአገራችን ማክሮ አኮኖሚ ሂደት የሚታዩ ተግዳሮቶችን በተለይም የውጭ ምንዛሪ አቅርቦት ችግርን እንዲታደግ ለማድረግ እንደ አንድ የልማት ፋይናንስ አማራጭ ዘዴ በመውሰድ የተቀየሰ የህግ ማዕቀፍ ነው። የተጠቀሰውን ዓላማ ለማሳካት ከተለያዩ ሀገራት መንግሥታት ጋር በሚኖር የኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ አማካኝነት እንዲሁም ከውጭ ባለሀብቶች ጋር በሚደረግ ግንኙነት ለአገር እና ሊህዝብ ጠቀሜታ ያላቸው የፕሮጀከት ሀሳቦቸን በቀጥታ ድርድር መተግበር ጠቃሚ መሆኑ የታመነበት ቢሆንም አሁን በስራ ላይ ያለው አዋጅ ይህን አሰራር የማይፈቅድ በመሆኑ አዋጁን ማሻሻል አስፈላጊ ሆኗል። ምክር ቤቱም በረቂቅ የማሻሻያ አዋጁ ላይ በሰፊው ከተወያየ በኋላ ግብአቶችን በማከል ይፀድቅ ዘንድ ወደ ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መርቶታል።
 
የቪዲዮ መረጃዎቻችንን ለማግኘት ትክክለኛውን የዩቲዩብ ቻናላችንን ሰብስክራይብ ያድርጉ
ፈጣን መረጃዎችን ለማግኘት ትክክለኛውን የቴሌግራም ቻናላችንን ይቀላቀሉ
የተመረጡ አጫጭር የቪዲዮ መረጃዎቻችንን ለማግኘት ትክክለኛውን የቲክቶክ አካውንታችንን ይከተሉ

አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ

ግብረመልስ
Top