Search

ቨርቹዋል የቱሪስት መረጃ ማዕከል በቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ሊገነባ ነው

ሓሙስ ሰኔ 25, 2018 50

ወደ ኢትዮጵያ የሚገቡ የውጭ ሀገራት ጎብኚዎች ስለ ሀገራችን የቱሪስት መዳረሻዎች በቂ መረጃ የሚያገኙበት ዘመናዊ የቨርቹዋል ማዕከል በአዲስ አበባ ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ መንገደኞች መውጫ ስፍራ ላይ ሊገነባ መሆኑ ተገለፀ።

ይህንን ዘመናዊ አገራዊ የመረጃ ማዕከል በጋራ ለመገንባት የሚያስችለውን ስምምነት የቱሪዝም ሚኒስቴር ከቶፓን ኢትዮጵያ (Topan Ethiopia) ከተባለ ተቋም ጋር በይፋ ተፈራርሟል።

በፊርማ ሥነ ሥርዓቱ ላይ የቱሪዝም ሚኒስትር ዴዔታ አቶ ስለሺ ግርማ እና የቶፓን ኢትዮጵያ ተወካይ ቃልኪዳን አረጋ የጋራ መግባቢያ ሰነዱን ተለዋውጠዋል።

 

በተደረሰው ስምምነት መሠረት ለዲጂታል ማዕከሉ ግንባታ የሚያስፈልገውን አጠቃላይ ወጪ ሁለቱ ተቋማት በጋራ የሚሸፍኑት ሲሆን፣ የቴክኖሎጂ ማዕከሉን የመገንባትና እውን የማድረግ ኃላፊነት ደግሞ ለቶፓን ኢትዮጵያ ተሰጥቷል።

ይህ በዓይነቱ ልዩ የሆነ የቨርቹዋል መረጃ ማዕከል በቀጣይ አሁን እየተገነባ በሚገኘው አዲሱ ትልቅ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ውስጥም ተካቶ አገልግሎት እንዲሰጥ እንደሚደረግ ከሚኒስቴሩ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።