ሁሉንም የመንግሥት አገልግሎቶች በአንድ ማዕከል የሚያገናኘውና በአፍሪካ የመጀመሪያው የሆነው ‘መሶብ’ (Unified App) ከተንቀሳቃሽ አውቶቡሶች በመውጣት በእያንዳንዱ ዜጋ የሞባይል ስልክ ላይ አገልግሎት መስጠት መጀመሩን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገልጸዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ "መሶብ የኢኮኖሚ ኢንፍራስትራክቸር ነው። ልክ መንገድ እና ኤርፖርት እንደምንለው ለአንድ ኢኮኖሚ ቁልፍ መሠረተ ልማት ነው" በማለት አሠራሩ ለዜጎች የሚሰጠውን የጊዜ ትርፍ በምሳሌ አስረድተዋል።

ቀደም ሲል ለዜጎች በ30 ደቂቃ ይሰጥ የነበረውን መታወቂያ አሁን በመሶብ አገልግሎት በ10 ደቂቃ ውስጥ መስጠት መቻሉንና ማትረፍ የተቻለው ጊዜ ወደ ኢኮኖሚ ምርታማነት እንደሚቀየር ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ በአንድ ዓመት ውስጥ 70 የ‘መሶብ’ ቅርንጫፎችን መክፈት መቻሏንና ይህ ስኬት ሌሎች የአፍሪካ ሀገራት በ10 እና 15 ዓመታት ውስጥ እንኳን ያላሳኩት መሆኑን ጠቅሰዋል።
አያይዘውም የሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን እና የ‘መሶብ’ የሥራ ኃላፊዎች ይህንን የቴክኖሎጂ ውጤት ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት በመሸጥ ለሀገራችን የውጭ ምንዛሬ እንዲያስገኙ አደራ ብለዋል።