ሀገራችን ኢትዮጵያ የ13ኛዋ ወር ጳጉሜን የመጀመሪያ ቀን በሆነው የእመርታ ቀን የሁለንተናዊ እድገቷን ፍሬዎች እና የተመዘገቡ ታሪካዊ ስኬቶችን በጋራ ታከብራለች።
ከእነዚህም የልማት እና የብልጽግና ስኬቶች መካከል በለውጥ ዓመታት የታየው የግብር አሰባሰብ ሥርዓት ከቢሊዮን ወደ ትሪሊዮን ብር ማደግ የሀገራችንን የኢኮኖሚ ሉዓላዊነትና የፋይናንስ ነፃነት ማረጋገጫ ታላቅ እመርታ ነው።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የ2018 በጀት ዓመት ሪፖርት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባቀረቡበት ወቅት እንደገለጹት፣ ኢትዮጵያ ባለፉት 27 ዓመታት በአጠቃላይ የሰበሰበችው ገቢ 1 ትሪሊዮን ብር እንኳን የማይሞላ የነበረ ቢሆንም፣ በ2018 በጀት ዓመት ብቻ ግን 1.5 ትሪሊዮን ብር ገቢ በመሰብሰብ ከ150% በላይ ታሪካዊ ብልጫ ያለው እመርታ ማስመዝገብ ተችሏል።
ይህ በምርት ቀን የምናከብረው ታሪካዊ ሽግግር የዲጂታል ቴክኖሎጂ አጠቃቀምን በማስፋፋት፣ የግብር ህጎችን በማሻሻል እና የታክስ መሠረቱን በማስፋት የተገኘ ታላቅ ውጤት ነው።
ግብር ከፋዮች በአካል ሳይገኙ በይነመረብን በመጠቀም ግብራቸውን የሚያስታውቁበትና የሚከፍሉበት የዲጂታል ታክስ ሥርዓት በመዘርጋቱ የታክስ ስወራን እና የቢሮክራሲ እንግልትን በእጅጉ መቀነስ ተችሏል።
በተጨማሪም አዳዲስ የንግድ ዘርፎችን ወደ ግብር ሥርዓቱ በማስገባትና ግብር መክፈል የሀገር ፍቅር መገለጫ ነው የሚል ባህል እንዲዳብር በማድረግ ሰፊ የገቢ መሠረት ተጥሏል።
የግብር ገቢ ከቢሊዮን ወደ ትሪሊዮን ማደጉ እንደ የኮሪደር ልማት፣ የትምህርትና ጤና መሰረተ ልማቶች እንዲሁም የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ግንባታን የመሳሰሉ ግዙፍ ሀገራዊ ፕሮጀክቶችን በራስ አቅም ለመሸፈን የሚያስችል አቅም በመፍጠሩ የጳጉሜን 1 የእመርታ ቀን አዲሱን የኢትዮጵያ የብልጽግና ምዕራፍ በግልጽ ያበስራል።
በአድማሱ አራጋው
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: