ከአውሮፓውያኑ መስከረም 12 እስከ 13 ቀን 2026 በኒው ዴልሂ በሚካሄደው 18ኛው የብሪክስ ጉባኤ ዋዜማ፣ ወደ ህንድ የፋይናንስ እና የፊንቴክ ዘርፎች የገባው የውጭ ካፒታል ፍሰት ከ13 ቢሊዮን ዶላር በላይ መድረሱ ይፋ ሆኗል።
እንደ ጃፓኑ ሚትሱቢሺ እና የተባበሩት አረብ ኤምሬትሱ ኤንቢዲ ያሉ ግዙፍ ዓለም አቀፍ ተቋማት በህንድ የባንክ ዘርፍ የወሰዱት ሰፊ ድርሻ፣ የብሪክስ አባል ሀገራት የቁጥጥር ስራቸውን ክፍት ሲያደርጉ የሚፈጠረውን ግዙፍ የካፒታል ማዕበል ግልጽ ማሳያ ነው።
ይህ የህንድ የባንክ አብዮት አፍሪካ በ1.4 ቢሊዮን ህዝቧ፣ በ3.4 ትሪሊዮን ዶላር የኢኮኖሚ አቅሟ እና በድንበር ተሻጋሪ ክፍያ ስርዓቷ አማካኝነት የራሷን የሃብት ማዕበል እንዴት ማረጋገጥ እንደምትችል የሚያሳይ ጠቋሚ ነው።
በዚህ አህጉራዊ እንቅስቃሴ ውስጥ የብሪክስ ሙሉ አባል የሆነችው ኢትዮጵያ፣ ራሷንም ሆነ አጠቃላይ አህጉሪቱን ተጠቃሚ የምታደርግበት ታሪካዊ እድል ከፊቷ ተቀምጧል።
ኢትዮጵያ የአፍሪካን ክፍያ ስርዓት ከብሪክስ ድንበር ተሻጋሪ የክፍያ ስልት ጋር እንዲያያዝ ሀሳብ በማቅረብ ጥገኝነትንና የግብይት ወጪን በከፍተኛ ደረጃ መቀነስ ትችላለች።
በተጨማሪም በአዲሱ ልማት ባንክ ውስጥ የአፍሪካ የመሰረተ ልማት እና የኃይል ማበልጸጊያ ፋሲሊቲ እንዲቋቋም በመገፋፋት፣ እንደ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ያሉ ግዙፍ ፕሮጀክቶችን በብሪክስ ካፒታል ማልማት ይቻላል።
የባንክ ዘርፏን ክፍት ማድረጓን ተንተርሶ ግዙፍ የብሪክስ ፈንዶችን መሳብ፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድን የሎጂስቲክስ መዋቅር ከብሪክስ የንግድ መስመሮች ጋር ማስተሳሰር እና ለሀገር ውስጥ ፊንቴክ ስታርት-አፖች የቴክኖሎጂ ሽግግር ማምጣት የኢትዮጵያ ዋነኛ ስልታዊ ጥቅሞች ናቸው።
የኒው ዴልሂው ጉባኤ ለአፍሪካ የካፒታል ማዕበል ተሞክሮን ወደ አህጉሩ የሚያመጣበት ወሳኝ አጋጣሚ ሲሆን፣ ኢትዮጵያ በብሪክስ ውስጥ ያላትን አባልነት እና አህጉራዊ ተቀባይነት በመጠቀም አፍሪካ ከብሪክስ ጋር የምታደርገውን የፋይናንስ ትስስር በባለቤትነት መምራት ይጠበቅባታል።
በሰለሞን ገዳ
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: