የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት ለመጠበቅ የተዘጋጀ ወታደራዊ አመራር ዓለም አቀፉዊ፣ አህጉራዊ እና ቀጣናዊ ጉዳዮችን በመረዳት፣ የሚመራውን አሀድ ሥነ ልቦናዊ ዝግጁነት ማረጋገጥ እንደሚባው የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ ጁላ ገለጹ።
ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ የማዕከላዊ ዕዝ መኮንኖች በግዳጅ አፈጻጸምና ቀጣይ አቅጣጫዎች ላይ የጋራ መግባባት በያዙበት መድረክ በቪድዮ ኮንፈረንስ ማጠቃለያ ሰጥተዋል።
መኮንኑ የጦሩን የዕለት ተለት ውስጣዊ አቅሞች በመፈተሽ ድል የሚፈጥር የሀገር ባለውለታ መሆኑን ያወሱት ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ፤ ሀገር እና ተቋም የሚረከበው ተተኪ መኮንን ፕሮፌሽናሊዝምን በመላበስ አመርቂ ግዳጅ እየፈጸመ ይገኛል ብለዋል።
የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት የድል አድራጊነቱ ምስጢር ዲሲፕሊኑ መሆኑን በማንሳትም፣ መኮንኑ አርዓያ በመሆን የሚያጋጥሙትን ፈተናዎች ሁሉ በብቃት ለመወጣት ዝግጁ ሊሆን እንደሚገባ መናገራቸውን ከኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ማኅበራዊ ትስስር ገፅ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የማዕከላዊ ዕዝ አዛዥ ሌተናል ጄኔራል ዘውዱ በላይ በበኩላቸው፣ ተቋሙ በተለያዩ ኮርሶች የሚያሰለጥናቸው መስመራዊ መኮንኖች ከቴክኖሎጂ ጋር የተግባቡ በመሆናቸው ተልዕኮን በአጭር ጊዜና በአነስተኛ ኪሳራ የመፈጸም ብቃታቸው ከፍ ያለ ነው ብለዋል።
ዕዙ ለማንኛውም ስምሪት አጋዥ የሆኑ የሠራዊት ግንባታ አቅጣጫዎችን በብቃት በማለፍ ለድል አስተማማኝ ቁመና ላይ እንደሚገኝ አረጋግጠዋል።