በአረንጓዴ አሻራ ልማት ሥራ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በ2015 ዓ.ም. የተከሏቸውን ችግኞች በየዕለቱ ሳይታክቱ በመንከባከብ ለፍሬ ስላበቁት ታታሪ አባት እንንገራችሁ።
አቶ ሲሳይ ታቦር በጌዴኦ ዞን የወናጎ ወረዳ ነዋሪ ሲሆኑ፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በ2015 ዓ.ም. በማሳቸው የተከሏቸውን ዘርፈ ብዙ ጥቅም ያላቸውን ችግኞች እንደ ልጅ በመንከባከብ ለፍሬ አብቅተዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በስፍራው ያኖሩትን አሻራ በማስቀጠል ለትውልድ የሚተላለፍ ነገር በመሥራታቸው ደስተኛ መሆናቸውን ይናገራሉ።
"ችግኝ እንደ ልጅ መንከባከብ ይፈልጋል" የሚሉት እኚህ አባት፣ በማሳቸው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከቀደማዊት እመቤት ዝናሽ ታያቸው ጋር የተከሏቸውን የቡና፣ የአቮካዶ እና የሙዝ ችግኞችን ተንከባክበው ከማሳደግ ባሻገር፣ 1.5 ሄክታር የቆዳ ስፋት ያለውን ማሳቸውን በአረንጓዴ አሻራ ችግኞች አልብሰዋል።
እንደ አቶ ሲሳይ ያሉ፣ ለትውልድ የተሻለ ከባቢን ለማስተላለፍ የሚተጉ ዜጎች ሊበረታቱ ይገባል።
በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ አነሳሽነት በ2011 ዓ.ም. በይፋ የተጀመረው የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር፣ ኢትዮጵያን አረንጓዴ የማልበስ እና ለተተኪው ትውልድ የበለጸገች ሀገር የማስረከብ ራዕይ ሰንቆ የተነሳ ታላቅ ሀገራዊ ንቅናቄ መሆኑ ይታወቃል።
በተመስገን ተስፋዬ