አዲስ አበባን እንደ ስሟ ውብና ለኑሮ ተስማሚ ለማድረግ የተገባውን ታሪካዊ ቃል በተግባር ለመተርጎም ባለፉት አምስት ዓመታት በርካታ መሠረታዊና ሥር-ነቀል ለውጦች መከናወናቸውን የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ አስታወቁ።
የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 4ኛ መደበኛ ጉባኤውን በዛሬው ዕለት ማካሄድ የጀመረ ሲሆን፤ በጉባኤው ላይ የ2018 በጀት ዓመት የዕቅድ አፈጻጸም ሪፖርትና የ2019 በጀት ዓመት ዋና ዋና የትኩረት አቅጣጫዎች ላይ ሰፊ ውይይት ተደርጓል።
ከንቲባ አዳነች አቤቤ ለምክር ቤቱ ያቀረቡትን የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት ተከትሎ፣ ከምክር ቤቱ አባላት ለተነሱ ጥያቄዎች ሰፊ ማብራሪያና ምላሽ የሰጡ ሲሆን፤ የቀረበው አጠቃላይ ሪፖርት በምክር ቤቱ ሙሉ ድምፅ ጸድቆ የመጀመሪያው ቀን ውሎ በስኬት መጠናቀቁ ታውቋል።
ከንቲባዋ በሪፖርታቸው፤ በከተማዋ ሥር ሰደው የነበሩ ኋላ ቀር አስተሳሰቦችንና ዘርፈ-ብዙ ችግሮችን በፅናት ተጋፍጦ በመለወጥ፣ መዲናዋን የልማት፣ የውበትና የሰላም አስተማማኝ ማዕከል ማድረግ ተችሏል ብለዋል።
በተለይም ባለፉት አምስት ዓመታት እንደ ‘ዓድዋ ድል መታሰቢያ’ ያሉ ትውልድ ተሻጋሪ ታላላቅ ፕሮጀክቶችንና መሠረተ-ልማቶችን በመገንባት፣ አሰባሳቢና ጠንካራ የወል ትርክቶችን በጋራ ለመቅረጽ ፅኑ መሠረቶች መጣላቸውን ገልጸዋል።
መዲናዋ ሰላሟን ዘላቂና አስተማማኝ፣ ውብ፣ ፅዱና አረንጓዴ በማድረግ ለኢትዮጵያውያን የብልፅግና እውነተኛ ተምሳሌትነቷን እያረጋገጠች መቀጠሏን የጠቆሙት ከንቲባዋ፤ ቀደም ሲል በከተማዋ እስከ 74 በመቶ ደርሶ የነበረውን ያልተደራጀና ኋላ ቀር የሻንቲ ገጽታ በተከናወኑ መጠነ-ሰፊ እንደገና የማልማትና የኮሪደር ሥራዎች ወደ 30 በመቶ ዝቅ ማድረግ መቻሉን ይፋ አድርገዋል።
ይህ ታሪካዊ እመርታ አዲስ አበባን ከአፍሪካ 10 ዋና ዋና ፅዱ ከተሞች አንዷ በማድረግ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ ዕውቅናና ክብር ያስገኘ መሆኑንም አክለዋል። ከዚህ ጋር ተያይዞም ቀደም ሲል 2.8 በመቶ ብቻ የነበረው የከተማዋ አጠቃላይ የአረንጓዴ ሽፋን በአምስት ዓመታት ውስጥ ወደ 24 በመቶ ከፍ እንዲል መደረጉን አስታውቀዋል።
በተቋማት ግንባታና በአገልግሎት አሰጣጥ ዙሪያም የከተማ አስተዳደሩ ነፃ፣ ገለልተኛና ብቁ የሆኑ ተቋማትን መገንባት ቁልፍ ስትራቴጂ አድርጎ በመሥራቱ የላቀ ውጤት መመዝገቡን አንስተው፤ ተቋማዊ አገልግሎቱ እንዲዘምን በተሰጠው ልዩ ትኩረት፤ ዋና መሥሪያ ቤትን ጨምሮ 11 የ"አዲስ መሶብ" የአንድ ማዕከል ዲጂታል የመንግሥት አገልግሎት መስጫ ማዕከላት ተከፍተው በሙሉ አቅማቸው በሥራ ላይ ይገኛሉ ብለዋል።
በእነዚህ ዘመናዊ ማዕከላት እስካሁን ለ263 ሺህ ተገልጋዮች ፈጣን አገልግሎት መስጠት የተቻለ ሲሆን፣ በማዕከላቱ የተመዘገበው የተገልጋዮች እርካታ በአማካይ 99 በመቶ መድረሱ ተረጋግጧል። ይህ የተገኘው ውጤት ለዘመናት በብልሹ አሠራር፣ በእንግልትና በተገልጋዮች ምሬት ይታወቅ ለነበረው ዘርፍ ትልቅና ታሪካዊ ስኬት መሆኑን ከንቲባ አዳነች አቤቤ ጠቁመው፤ ቀሪ የመንግሥት አገልግሎቶች በቀጣዩ አዲሱ የበጀት ዓመት ወደ ዲጂታል ሥርዓት እንደሚገቡ አስታውቀዋል።
በይመር አደም
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: