ኢቢሲ ዛሬ አስመርቆ ወደ ሥራ ያስገባው የፓርላማ ቻናል ሕብረ ብሔራዊት ኢትዮጵያን ለመገንባት ወሳኝ ሚና ይጫወታል ሲሉ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባዔ ታገሰ ጫፎ ተናገሩ።
አፈ ጉባዔ ታገሰ ጫፎ የኢቲቪ ፓርላማ ቻናልን በዛሬው ዕለት መርቀው በይፋ ሥራ አስጀምረዋል።
በዚህ ወቅት አፈ ጉባዔው እንደተናገሩት፤ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ለወከሉት ሕዝብ ድምፅ ለመሆን ሕዝቡ ደግሞ በበርካታ ጉዳዮች ላይ ያሉትን ሀሳብ፣ አስተያየት በነጻነት ለማስተላለፍ ሚዲያ አይነተኛ ሚና ይጫወታል፡፡ ለዚህ ደግሞ አዲሱ የኢቲቪ ፓርላማ ቻናል ጉልህ ድርሻ ይኖረዋል ነው ያሉት።
የኢቲቪ ፓርላማ ቻናል ሥርጭት መጀመር ሌላው ጥቅም የኢትዮጵያን መልክ መግለጡ ነው ያሉት አፈ ጉባኤው፤ ከተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች የተወጣጡ የሕዝብ ተወካዮች የመጡበትን አካባቢ ባህልና ቱውፊት በማስተዋወቅ ሕብረ ብሔራዊነትን ያጠናክራል ብለዋል።
የወል እና አሰባሳቢ ትርክቶቻችን ላይ በጋራ ለመስራት ቻናሉ ሰፊ ሥራ ይጠብቀዋል ያሉት አፈ ጉባኤው፤ ይህንንም በጋራ ሆነን የምንሰራው ይሆናል ሲሉ ነው አክለው የተናገሩት።
በሃብተሚካኤል ክፍሉ