የኢትዮጵያ የስታርት አፕ እና የሥራ ፈጠራ ምህዳር እንዲስፋፋ ከእስራኤል ጋር እየተሰራ መሆኖኑን በኢትዮጵያ የእስራኤል አምባሳደር አብርሃም ንጉሴ (ዶ/ር) ገልጸዋል፡፡
አምባሳደር አብርሃም ንጉሴ (ዶ/ር) ከኢቲቪ ጋር በነበራቸው ቆይታ፤ እስራኤል በስታርታ አፕ እና በሥራ ፈጠራ ያላትን እውቀት ለኢትዮጵያ ለማካፈል በትኩረት እየሰራች ትገኛለች ብለዋል፡፡
በዚህም እስራኤል በስታርት አፕ እና ሥራ ፈጠራ የተለያዩ ባለሙያዎችን ባለፉት ወራት ወደ ኢትዮጵያ መላኳን አንስተዋል፡፡
ሀገሪቱ ያላትን ተሞክሮ ለኢትዮጵያ ወጣቶች በማካፈል ሥራ ፈጣሪ እንዲሆኑ ድጋፍ እያደረገች መሆኗን አምባሳደር አብርሃም ተናግረዋል፡፡
እ.አ.አ በ2001 የተቋቋመው ዩኒስትሪም የተባለው ተቋም በእስራኤል የስታርት አፕ ሀሳብ ያላቸውን አዳጊዎች በማወዳደር ይሸልማል፡፡
የውድድር መድረኩ ከተለያዩ ሀገራት የግል ባለሐብቶች እንዲሁም ከፍተኛ የመንግስት የሥራ ኃላፊዎች የሚታደሙበት በመሆኑ፣ ለተወዳዳሪዎቹ የሥራ እና ድጋፍ የሚያገኙበትን እድል ይፈጥርላቸዋል፡፡
የእስራኤል ሀገር አዳጊዎች የሚታቀፉበት የስታርት አፕ ፕሮጀክቶች አመርቂ ውጤት በማስገኘታቸው፣ ኢትዮጵያም ከዚህ ተሞክሮ መውሰድ እንደሚገባት በኢትዮጵያ የስቲም ፓወር ዋና ዳይሬክተር ስሜነው ቀስቅስ (ዶ/ር) ገልጸዋል፡፡
ኢትዮጵያም አሁን ላይ ለስታርት አፕ ምህዳሩ ትኩረት በመስጠት ከዚህቀደም የኢትዮጵያ እና ምሥራቅ አፍሪካ ስታርት አፕ ውድድር ሽልማት ማዘጋጀቷን አንስተው፤ በቀጣይም የስታርት አፕ ሀሳብ ውድድሮች እንደሚዘጋጁ አመላክተዋል፡፡
በሜሮን ንብረት