በመካከለኛው ምስራቅ አሜሪካ እና እስራኤል ከኢራን ጋር የገቡበት ጦርነት በአውሮፓ አየር መንገዶች ላይ የነዳጅ አቅርቦት እጥረት ስጋት ደቅኗል።
ይህንን ችግር ለመቅረፍም የአውሮፓ ኅብረት ልዩ የመፍትሄ ዕቅድ እያዘጋጀ መሆኑን የህብረቱ ባለሥልጣናት መግለጻቸውን ሮይተርስ ዘግቧል።
ኅብረቱ የነዳጅ ማጣሪያዎችን የማምረት አቅም ለማሳደግና የአቅርቦት ሰንሰለቱን ለማረጋጋት የሚያስችል ረቂቅ ሰነድ እያዘጋጀ ይገኛል።
የአውሮፓ ኮሚሽን ከሚቀጥለው ወር ጀምሮ በአባል ሀገራቱ የሚገኙ የነዳጅ ማጣሪያዎችን የማምረት አቅም በዝርዝር የሚያጠና ሲሆን፣ ያሉትን ማጣሪያዎች ሙሉ በሙሉ ጥቅም ላይ እንዲውሉ የሚያስችሉ እርምጃዎችን ይወስዳል ተብሎ ይጠበቃል።
አውሮፓውያን 75 በመቶ የአውሮፕላን ነዳጅ የሚያስመጡት ከመካከለኛው ምስራቅ በመሆኑ፣ ኅብረቱ አሁን ላይ የገጠመውን እጥረት ለመቅረፍ አማራጭ መፍትሄዎችን ለመመልከት ተገዷል።
ዓለም አቀፉ የኢነርጂ ኤጀንሲ (IEA) በበኩሉ አውሮፓ ከመካከለኛው ምስራቅ የሚያገኘውን ነዳጅ ቢያንስ በግማሽ መተካት ካልቻለ፣ እስከ ሰኔ ወር ድረስ የክረምቱን የጉዞ ወቅት የሚያስተጓጉል ከፍተኛ እጥረት ሊያጋጥመው እንደሚችል ስጋቱን ገልጿል።
በመሀመድ ፊጣሞ