በአንድ ወቅት ከ40 በመቶ በላይ የነበረው የኢትዮጵያ የደን ሽፋን፣ ባለፉት አሥርት ዓመታት ዘላቂነት በሌለው አጠቃቀም፣ በዛፍ ቆረጣ እና በተዛባ የመሬት አስተዳደር ሳቢያ ወደ 3 በመቶ ዝቅ ብሎ ነበር።
ይህ የደን መመናመን የብዝኃ ሕይወት መጥፋትን፣ የመሬት መደህየትን፣ የምርታማነት ማሽቆልቆልንና የውኃ አካላት በደለል መሞላትን አስከትሎ ማኅበረሰባችንን ለከፋ ድርቅ፣ ጎርፍና የምግብ ዋስትና ችግር አጋልጦት ቆይቷል።
የተባበሩት መንግሥታት የአካባቢ ጥበቃ ፕሮግራም (UNEP)፣ እ.አ.አ ከ1973 ጀምሮ በየዓመቱ ግንቦት 28 የሚከበረውን የዓለም የአካባቢ ጥበቃ ቀን የሰየመውም ሥነ-ምህዳራዊ ቀውስን ለመታደግ ነው።
ዘንድሮ በአዘርባጃን አስተናጋጅነት የተከበረው ዕለቱ ትኩረቱን በአየር ንብረት ለውጥ ላይ ያደረገ ሲሆን፤ የሰው ልጅ ዓመታዊ የበካይ ጋዝ ልቀትን እ.አ.አ በ2030 በግማሽ መቀነስ ካልቻለ ሥነ-ምህዳሩ ሊሽመደመድ እንደሚችል የሳይንስ ሊቃውንት ያስጠነቅቃሉ።
ኢትዮጵያ ይህን ስጋ በተግባር ለመቀልበስ በ2011 ዓ.ም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት "የአረንጓዴ ዐሻራ" የችግኝ ተከላ ንቅናቄን በይፋ ጀምራለች።
መርሐ ግብሩ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ የሌለው አፈጻጸም ያስመዘገበ ሲሆን፣ በሀገር አቀፍ ደረጃም ክንውኑ በየዓመቱ ክብረ ወሰን በከፍተኛ ልዩነት የተሻሻለበት ነው፦
በ2011 ዓ.ም፦ 4.7 ቢሊዮን ችግኝ
በ2012 ዓ.ም፦ 5.9 ቢሊዮን ችግኝ
በ2013 ዓ.ም፦ 6.8 ቢሊዮን ችግኝ
በ2014 ዓ.ም፦ 7.2 ቢሊዮን ችግኝ
በ2015 እና 2016 ዓ.ም፦ እያንዳንዳቸው 7.5 ቢሊዮን ችግኝ
በ2017 ዓ.ም፦ 8 ቢሊዮን ችግኝ
በ2018 ዓ.ም (የዘንድሮ ዕቅድ)፦ 8.5 ቢሊዮን ችግኝ
በአጠቃላይ እስካሁን ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞች የተተከሉ ሲሆን፣ ይህም በመጀመሪያው እና በሁለተኛው ምዕራፍ ማጠናቀቂያ ላይ የተቀመጠውን 50 ቢሊዮን ችግኝ የመትከል ግብ ለማሳካት የቀረው ጥቂት ነው።
የግብርና ሚኒስቴር እና የምርምር ተቋማት ጥናቶች እንዳረጋገጡት፤ የኢትዮጵያ የደን ሽፋን በጥቂት ዓመታት ውስጥ ከ17.2 በመቶ ወደ 23.6 በመቶ አድጓል። ይህ ስኬት የተገኘው የደን፣ የፍራፍሬ፣ የመኖ እና የማገዶ ዛፎች በጥናት በመተከላቸው ነው።
ከተተከለው ችግኝ መካከል 30 በመቶው በዓባይ ተፋሰስ እንዲሁም በአዋሽ እና በስምጥ ሸለቆ ውስጥ መተከሉም የከርሰ ምድር ውኃ መጠንን ከፍ አድርጎታል።
ይህም አርሶ አደሩ የአየር ንብረት ለውጥን እንዲቋቋም እና የምግብ ዋስትናውን እንዲያረጋግጥ እያስቻለው ይገኛል።
የአረንጓዴ ዐሻራ ንቅናቄ ቀጣናዊ ዲፕሎማሲንም ያጠናከረ ሲሆን፣ ኢትዮጵያ ለጅቡቲ የችግኝ አቅርቦት በማድረግ የበረሃማነት መስፋፋትን በጋራ የመከላከል አዲስ ምዕራፍ ከፍታለች፤ ለፓኪስታንም ተሞክሮዋን አካፍላለች።
ከዚህም በላይ ወደ 23.6 በመቶ ያደገው የደን ሽፋን በዓለም አቀፉ የካርበን ገበያ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ የሚያስገኝ ወርቃማ የኢኮኖሚ በር ከፍቷል።
መንግሥት ከግብርና ትራንስፎርሜሽን ተቋማትና ከሳይንስ አካዳሚ ጋር በመቀናጀት በማስረጃና በእውቀት እየመራው ያለው የአረንጓዴ ዐሻራ ሥራ፣ የሀገራችንን የምግብ ሉዓላዊነት የሚያረጋግጥ ታላቅ የትውልድ ፕሮጀክት መሆኑን በተጨባጭ አስመስክሯል።