በ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ አብላጫ ድምፅ አግኝቶ ያሸነፈው የፖለቲካ ፓርቲ ሀገርን እና ሕዝብን የሚጠቅሙ አጀንዳዎችን ለይቶ መሥራት እንደሚጠበቅበት የታርጫ ከተማ ነዋሪዎች ገልፀዋል።




ኢቢሲ ያነጋገራቸው የከተማዋ ነዋሪዎች በኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ሂደት ላይ የነቃ እና ነፃ ተሳትፎ ማድረግ መቻላቸው የተሻለች ኢትዮጵያን ለመገንባት የተጣለ ጠንካራ መሠረት መሆኑን ገልጸዋል።
በምርጫው አብላጫ ድምፅ አግኝቶ ያሸነፈው የፖለቲካ ፓርቲ ሀገርንና ሕዝብን የሚጠቅሙ አጀንዳዎችን ለይቶ ከመሥራት ባለፈ፤ በየአካባቢው የተጀመሩ የልማት ሥራዎችን ወደ ውጤት የመቀየር፣ ሀገራዊ ሰላም እና አንድነትን የማጎልበት ተግባር ላይ በትኩረት ሊሠራ እንደሚገባ አመላክተዋል።
ከዚህ በተጨማሪም ለወጣቶች የሥራ ዕድልን የማመቻቸት፣ የኑሮ ውድነትን የማረጋጋት እና የሕግ የበላይነትን ይበልጥ የማጠናከር ሥራዎች ትኩረት ሊሰጣቸው እንደሚገባ የገለጹት የታርጫ ከተማ ነዋሪዎች፤ በቀጣይ ከሚመሠረተው መንግሥት ጋር በጋራ ለመሥራት ሙሉ ዝግጁ መሆናቸውን ጠቁመዋል።
በሰለሞን ባረና