በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በቅርቡ የፀደቀው የቁልፍ መሠረተ ልማቶች የሳይበር ደኅንነት አዋጅ የኢትዮጵያን የዲጂታላይዜሽን ጉዞ በጠንካራ የደኅንነት መሠረት ላይ ለመገንባት ትልቅ አቅም እንደሚፈጥር የኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት አስተዳደር (ኢንሳ) ዋና ዳይሬክተር ትዕግስት ሃሚድ ገለጹ።
ዋና ዳይሬክተሯ አዲሱን አዋጅ አስመልክተው በሰጡት መግለጫ፣ አዋጁ የሀገርን ስትራቴጂካዊ ጥቅም ማዕከል ያደረገ የጥበቃ ሥርዓት ለመዘርጋት 12 የቁልፍ መሠረተ ልማት ዘርፎችን ለይቶ የተቀመጠ መሆኑን አስታውቀዋል።
በአዋጁ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂና ኮሙኒኬሽን፣ የፋይናንስ፣ የፀጥታና ደኅንነት፣የትራንስፖርት፣ የትምህርት፣ የጤና፣ የውሃና ኢነርጂ፣ የመንግሥት አገልግሎቶች፣ የአደጋ መከላከል አገልግሎቶች፣ ግብርና እንዲሁም ንግድና ኢንዱስትሪ ዘርፎችን ያካተተ መሆኑ ተመላክቷል።
በተጨማሪም አዋጁ የቁልፍ መሠረተ ልማት ባለቤቶች ሊወጧቸው የሚገቡ 18 ዋና ዋና የሳይበር ደኅንነት ግዴታዎችን ማስቀመጡ ተገልጻል።
አዋጁ ሙሉ ለሙሉ ወደ ሥራ ከመግባቱ በፊት ተቋማት አስፈላጊውን ዝግጅት በማድረግ ቴክኖሎጂያቸውን የተጠበቀ እንዲያደርጉ ዋና ዳይሬክተሯ አሳስበዋል።
አስተዳደሩ በዚህ የሽግግር ወቅት አስፈላጊውን መመሪያ በማዘጋጀትና የቴክኒክ ድጋፍ በመስጠት ረገድ ቁልፍ ሚና እንደሚጫወትም አረጋግጠዋል።
ይህ አዋጅ የቁልፍ መሠረተ ልማት ተቋማትን የሳይበር ደኅንነት ለማጠናከር፣ የሳይበር ጥቃቶችን ለመከላከል እንዲሁም መልካም አስተዳደርና ፍትህን ለማስፈን ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለው አመላክተዋል።
በአባዲ ወይናይ
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: