Search

ጥማድ በሬን በአነስተኛ የእርሻ ትራክተር ለመተካት እየተጋ ያለው ማህበር

Aug 19, 2025

ወጣት ጋሻው ኤዶም ይባላል። የሀዋሳ ከተማ ነዋሪ ነው። በመካኒካል ምህንድስና ትምህርቱን ካጠናቀቀ በኋላ የመንግሥት ስራን ከመፈለግ ይልቅ በሀዋሳ ከተማ በማህበር በመደራጀት ወደ ማሽን ማምረት ስራ ገባ።
ኢትዮጵያውያን ያለንን ሀብት በአግባቡ ባለመጠቀማችን ከትንንሽ እስከ ትልልቅ ማሽኖችን ከውጭ እያስገባን ቆይተናል የሚለው የኤልሻሎም ጠቅላላ የኤሌክትሮ መካኒካል ኢንጂነሪንግ ማህበር ስራ አስኪያጅ አቶ ጋሻው፤ ማህበሩ ባለፉት 9 ዓመታት የተለያዩ ማሽነሪዎችን በማምረት ለተለያዩ ግለሰቦች እና ተቋማት ማቅረቡን ይገልጻል።
ማህበሩ በኢትዮጵያ የተለያዩ አካባቢዎች ያሉ አርሶአደሮችን ህይወት በቀላል ማሽነሪዎች ማዘመን እና ትርፋማ ማድረግ ይቻላል የሚል አቋም በመያዝ የተለያዩ የግብርና መሳሪያዎችን እያመረተ ነው።
ጋሻው እና ጓደኞቹ የሰሩት የእርሻ ትራክተር የትኛውም አርሶአደር በራሱ ሊያንቀሳቅሰው የሚችል ሲሆን በቀን እስከ አራት ሄክታር ማሳ ማረስ ያስችላል።
ማህበሩ አሁን ላይ ከብዙ ውጣውረድ በኋላ የእርሻ ትራክተርን ጨምሮ፣ የእህል መውቂያ፣ የቡና መቁያ እና መፍጫ፣ የዳቦ መጋገሪያ እንዲሁም የጂም ቤት ዕቃዎችን በማምረት ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ እየተካ ነው።
ወጣት ጋሻው ማህበራዊ ሚዲያው የፈጠረውን ዕድል እንደ ገበያ በመጠቀም፤ ማህበሩ አዳዲስ ፈጠራዎችን ይማራል፤ ምርቱን ያስተዋውቃል፤ ትዕዛዝ ተቀብሎ ይሰራል ሲል ገልጿል።
ሌሎች ወጣቶችም ወቅቱ የፈጠረውን ዕድል በመጠቀም እና ለሚያጋጥሟቸው ችግሮች ባለመሸነፍ ትልቅ ሀብት መፍጠር እንደሚችሉም ወጣት ጋሻው ምክሩን ለግሷል።
በአስረሳው ወገሼ