የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በልዩ ልዩ የስፖርት ዘርፎች የላቀ ውጤት ላስመዘገቡ የክለቡ ስፖርተኞች፣ አሰልጣኞች እና አመራሮች የከፍተኛ እውቅና፣ የምስጋና እና የሽኝት መርሐ ግብር አከናውኗል።
በዘንድሮው የካፍ የሴካፋ ዞን የሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ ማጣሪያ ኢትዮጵያን በመወከል ለሚወዳደረው የባንኩ የሴቶች እግር ኳስ ቡድን በተደረገው የሽኝት ፕሮግራም ላይ የባንኩ ከፍተኛ አመራሮች እና የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት ኢሳያስ ጂራ ተገኝተዋል።
የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ስፖርት ማህበር በኢትዮጵያ ስፖርት ታሪክ ውስጥ ጉልህ ስሙን ያሠፈረ ግዙፍ ተቋም ነው። የባንኩ የሴቶች እግር ኳስ ቡድን በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ታሪክ ለ6 ተከታታይ ዓመታት፣ በጥቅሉ ደግሞ ለ9 ጊዜያት የሊጉ ሻምፒዮን መሆን ችሏል።
ማህበሩ በስሩ ባቀፋቸው ልዩ ልዩ የስፖርት ቡድኖች አማካይነት በ2017 ዓ.ም እና በ2018 ዓ.ም ሁለት የውድድር ዓመታት ብቻ በድምሩ 59 ዋንጫዎችን በመሰብሰብ ታሪክ ሠርቷል።
የስፖርት ማህበሩ አሁን ላይ በስሩ 8 ልዩ ልዩ የስፖርት ቡድኖችን ያቀፈ ሲሆን፣ ከ300 በላይ ለሚሆኑ ወጣት ስፖርተኞች እና ባለሙያዎች የሥራ ዕድል በመፍጠር ማህበራዊ ኃላፊነቱን እየተወጣ ይገኛል።
የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ መሠረት ደፋር፣ ገብረእግዚአብሔር ገብረማርያም እና ወርቅነሽ ኪዳኔን ጨምሮ በኦሎምፒክ አደባባይ የሀገራቸውን ስም ያስጠሩ ድንቅ አትሌቶችን ማፍራት የቻለ ነው።
ባንኩ ካፈራቸው ሌሎች ስመጥር ስፖርተኞች መካከል የኦሪገን ከ20 ዓመት በታች የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮኗ ዮርዳኖስ ጥጋቡ እና የኢትዮጵያ ሴቶች እግር ኳስ ምልክት የሆነችው ሎዛ አበራ ተጠቃሽ ናቸው።
ባንኩ በሀገራችን የኢኮኖሚ ዘርፍ እየተጫወተው ያለውን ቁልፍ ሚና ወጣቶችን በማብቃት በስፖርቱ ዘርፍም ለመድገም በትጋት እንደሚሠራ ገልጿል።
በሐና ምንዳሁን
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: