በአሜሪካ እና በኢራን መካከል ለሦስት ወራት የዘለቀውን ወታደራዊ ግጭት ለማስቆም የተደረሰው ጊዜያዊ የመግባቢያ ስምምነት ይፋዊ የአገልግሎት ጊዜው ተጠናቋል።
ሁለቱም ወገኖች ላለፉት ሳምንታት የስምምነቱን ውሎች ጥሳችኋል በሚል እርስ በርሳቸው ሲካሰሱ የቆዩ በመሆኑ፣ ሰነዱን ለማራዘምም ሆነ አዲስ ድርድር ለመጀመር ያላቸው ፍላጎት እጅግ ዝቅተኛ ደረጃ ላይ መድረሱ ታውቋል።
የዚህ ስምምነት ውድቀት መሠረታዊ መንስኤ ከሁለቱ ሀገራት ስትራቴጂካዊ የፅንሰ-ሀሳብ ልዩነት የመነጨ ነው። ኢራን ይህንን ስምምነት የጦርነቱ ፍጹም ማብቂያ፣ የማዕቀቦች መነሻ እና የታገዱ ሀብቶች መለቀቂያ አድርጋ ስትወስደው፣ አሜሪካ በበኩሏ ተጨማሪ የኑክሌር ግዴታዎች የሚጣሉበት ጊዜያዊ የተኩስ ማቆም አድርጋ ተመልክታዋለች።
ከተፈራረሙት ሰነድ በተቃራኒ የተጣሉ ማዕቀቦች አለመነሳታቸው፣ የባህር ከበባው አለመላላቱ እና ሁለቱም ወገኖች የፈጸሟቸው የአጸፋ ጥቃቶች ስምምነቱን በተግባር ዋጋ ቢስ አድርገውታል።
ይህ የስምምነት ማብቃት በሁለቱም ሀገራት ደህንነትና ወታደራዊ አቋም ላይ ስር ነቀል ለውጥ አምጥቷል። ኢራን ከዚህ ቀደም ትከተለው የነበረውን ተከላካይ አቋም ወደ አጥቂ የመከላከል ስትራቴጂ መቀየሯን ይፋ ያደረገች ሲሆን፣ ይህም በሆርሙዝ ሰርጥ ላይ ያለባትን ወታደራዊና ጂኦ-ፖለቲካዊ ተፅዕኖ ለማስከበር ያላትን ቁርጠኝነት በግልፅ ያሳያል።
በሌላ በኩል አሜሪካ በውሃ መንገዱ ላይ ጠንካራ የባህር ኃይል ቁጥጥር ለማድረግና አዳዲስ ማዕቀቦችን ለመጣል ብትዝትም፣ የዓየር መከላከያ ሚሳይሎች መቀነስ እና የስምሪት መራዘም ወታደራዊ አማራጮቿን ውስን እንዳደረገው ተመላክቷል።
ይህ ወታደራዊና ፖለቲካዊ ውጥረት በዓለም አቀፍ የነዳጅ ንግድና ኢኮኖሚ ላይ እያሳደረ ያለው ተፅዕኖ እጅግ ከፍተኛ ሆኖ ቀጥሏል። በሆርሙዝ ሰርጥ የሚያልፈው የንግድና የነዳጅ መርከቦች እንቅስቃሴ በከፍተኛ ሁኔታ የቀነሰ ሲሆን፣ በቅርብ ቀናት የተፈጸሙ ጥቃቶች እና የባህር ከበባዎች ስጋቱን አብዝተውታል።
ባለሙያዎች እንደሚተነብዩት ሁለቱም ሀገራት በኃይል ወይም በኢኮኖሚ ጫና አንዱ ሌላውን ሙሉ በሙሉ ማስገደድ የማይችሉበት ደረጃ ላይ ደርሰዋል።
በመሆኑም የሆርሙዝ ሰርጥ ውጥረት እና የሁለቱ ሀገራት ግጭት ዘላቂ መፍትሔ ሊያገኝ የሚችለው ሁለቱም ወገኖች ከፍተኛ ዋጋ ከተከፋፈሉ በኋላ፣ የየራሳቸውን ሀገራዊና ቀጣናዊ ጥቅሞች ያገናዘበ አዲስ ስትራቴጂካዊ ድርድር ሲያደርጉ ብቻ እንደሚሆን የፖለቲካ ተንታኞች ያስገነዝባሉ።
በሰለሞን ገዳ
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: