የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል የቀጣናውን ሀገራት በብርሃን ገመድ እያስተሣሠረ፣ ለሀገርም የውጭ ምንዛሪ እያስገኘ ነው።
ኢትዮጵያ በጨለማ ውስጥ ለነበሩ መንደሮች ብርሃን፣ ለቆሙ ኢንዱስትሪዎች ሕይወት፣ ለቀጣናው ኢኮኖሚ ደግሞ አዲስ ጉልበት እየሆናት ይገኛል።
በ2016 ዓ.ም ኢትዮጵያ ከኤሌክትሪክ ወጪ ንግድ ያገኘችው ገቢ 133 ሚሊዮን ዶላር ነበር። ይህ ቁጥር ለተቋሙ ጥሩ መነሻ ቢሆንም፣ ከሀገራችን የኃይል አቅም ጋር ሲነጻጸር ገና የመንገዱ መጀመሪያ ነበር።
ነገር ግን በ2017 ዓ.ም ነገሮች በከፍተኛ ፍጥነት ተቀየሩ። ገቢው ከሁለት እጥፍ በላይ በመጨመር 374 ሚሊዮን ዶላር ደረሰ። ዕድገቱ የመሠረተ ልማቶች መሟላት እና የአዳዲስ መስመሮች መከፈት ውጤት ነው።
በ2018 ዓ.ም ገቢው ወደ 476 ሚሊዮን ዶላር ከፍ ማለት ችሏል። በሦስት ዓመታት ውስጥ ብቻ ገቢው ከ133 ሚሊዮን ወደ 476 ሚሊዮን ዶላር አድጓል! ይህ ማለት የ350% ገደማ ዕድገት ነው።
ከኤሌክትሪክ የሚገኘው ግማሽ ቢሊዮን ዶላር ሊቃረብ የቻለው ገቢ ለኢኮኖሚው ትልቅ አቅም ይፈጥርለታል፤ የመተንፈሻ ካርታም ሆኗል።
የሕዳሴው ግድብ ተርባይኖች ኃይል ማመንጨት መጀመራቸው እና እንደ ጊቤ 3 ያሉ ታላላቅ የኃይል ማመንጫዎች በሙሉ አቅማቸው መሥራታቸው ሀገራችን ለሀገር ውስጥ የሚበቃ ብቻ ሳይሆን ለኤክስፖርት የሚተርፍ ትርፍ ኃይል እንድታመነጭ አድርጓታል።
ኢትዮጵያ ወደ ጎረቤት ሀገራት የዘረጋቻቸው የከፍተኛ ኃይል ማስተላለፊያ መስመሮች የቀጣናውን ገበያ እንድትቆጣጠር አስችለዋታል።
ኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ለጎረቤቶቿ ስትሸጥ የምታገኘው የዶላር ምንዛሪ ብቻ አይደለም። ሀገራችን በቀጣናው ላይ የሚኖራት ጂኦ-ፖለቲካዊ ተጽዕኖ በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ ይገኛል።
ጅቡቲ፣ ሱዳን፣ ኬንያ፣ እንዲሁም ታንዛኒያ እና ደቡብ ሱዳን እነዚህ ሀገራት የኢንዱስትሪዎቻቸውን፣ የሆስፒታሎቻቸውን እና የከተሞቻቸውን መብራት ከኢትዮጵያ ጋር አያይዘዋል።
አንድ ሀገር የሌላውን ሀገር የኃይል ፍላጎት ሲያሟላ፣ በመካከላቸው ያለው ግንኙነት ከንግድ ያልፋል፤ የጋራ ደኅንነት እና የተሳሰረ ኢኮኖሚ ይፈጠራል።
ይህ ጉዞ ይቀጥላል፤ ከ476 ሚሊዮን ዶላር አልፎ ወደ ቢሊዮን ዶላሮች የሚደረገው ጉዞ በጽናት የሚቀጥል ይሆናል።
በንብረቴ ተሆነ
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: