በክረምቱ የበጎ ፈቃድ መርኃ ግብር ከፍለው ህክምና ማግኘት ለማይችሉ ከ5 ሚሊዮን በላይ ዜጎች ነፃ ህክምና መስጠት መቻሉን የጤና ሚኒስትር ዶ/ር መቅደስ ዳባ አስታውቀዋል፡፡
ሚኒስትሯ ይህን የገለፁት ውዳሴ ዲያግኖስቲክ ማዕከል "ጳጉሜን ለጤና" በሚል መርህ ከፍለው ህክምና ማግኘት ለማይችሉ የማህበረሰብ ክፍሎች ነፃ ህክምና ሊሰጥ መሆኑን ባስታወቀበት መርኃ ግብር ላይ ነው፡፡
ማዕከሉ ያለፉትን 15 ዓመታት ያዳበረው ይህ ልምዱ የሚያስመሰግነው መሆኑን የገለፁት ዶ/ር መቅደስ ዳባ፤ በተለይም በመርኃ ግብሩ ተቋማትን ማደስ እና የጤና ባለሙያዎች የህክምና እገዛ እንዲያገኙ ለማድረግ መታቀዱ የሚበረታታ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
የበጎ ፈቃድ አገልግሎት በርካታ እመርታ እያስመዘገበ መሆኑን የገለፁት ሚኒስትሯ፤ ይህ ከመንግስት ባሻገር የግል ተቋማት የራሳቸውን ማህበራዊ ኃላፊነት የሚወጡበት ጉዳይ መሆኑን ገልፀዋል፡፡
መንግስት ከግል ተቋማት ጋር የሚደረጉ ትብብሮች ላይ በትኩረት እንደሚሰራና በቀጣይም በዚሁ ዘርፍ በጋራ ለመስራት ዝግጁ መሆኑን አረጋግጠዋል፡፡
በአፎምያ ክበበው
#ebc #ebcdotstream #mohethiopia #WDC