የዝናብ እጥረት በተደጋጋሚ በድርቅ እንዲፈተን አድርጎት የነበረው የቦረና ዞን በአዲስ ምዕራፍ ላይ ይገኛል ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ፡፡
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በኦሮሚያ ክልል ቦረና ዞን የተለያዩ የልማት ስራዎችን የጎበኙ ሲሆን፣ በጉብኝቱ የቦረና አርብቶ አደሮች በተገኘው ለውጥ መደሰታቸውን ተመልክተናል ብለዋል በማህበራዊ የትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት፡፡
በዞኑ በተደጋጋሚ ለሚከሰተው ድርቅ ዘላቂ መፍትሔን ለማበጀት በተጀመረው ፊና ፕሮጀክት 14 ግድቦች መገንባታቸው፣ የአርብቶ አደሩ የውኃ እና የመኖ እጥረት እንዲቀረፍ ማስቻሉን ተናግረዋል፡፡
ፊና ውኃን፣ መሬትን፣ ግጦሽን ማስተዳደርና ከሕይወት ጋር አያይዞ ዘላቂ መፍትሔ እንዲሰጡ ማስቻል ነው፤ ይህንን ደግሞ የቦረና ህዝብ በተግባር ማሳየት ችሏል ነው ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፡፡
ዛሬ የቦረና አርብቶ አደሮች የድርቅ ስጋት የለባቸውም ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ለከብቶች በቂ ውኃ እና መኖ መኖሩን ጠቅሰው፤ በዞኑ ሁሉም ሙሉ ነው ብለዋል፡፡
የቦረና ህዝብ ለሌሎችም ጭምር ምሳሌ የሚሆን ስራ መስታቱን ገልጸው፤ ይህንን ተግባራዊ ላደረጉ በየደረጃው ለሚገኙ አመራሮች እና ለቦረና ህዝብ ምስጋና አቅርበዋል፡፡