የሩሲያው ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን እና የሰሜን ኮሪያው መሪ ኪም ጆንግ ኡን በቻይና ወታደራዊ ትርዒት ላይ ከታደሙ በኋላ በቤጂንግ ውይይት አድርገዋል።
በውይይቱ ወቅት፤ የሩሲያው ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን የሰሜን ኮሪያ ወታደሮች ከሩሲያ ጦር ጎን ሆነው ላበረከቱት አስተዋፅኦ ምስጋና አቅርበዋል።
የሰሜን ኮሪያ ወታደሮች በሩሲያ ዩክሬን ጦርነት በድፍረት እና በጀግንነት ተዋግተዋል ሲሉም ተናግረዋል።
የሰሜን ኮሪያው መሪ ኪም ጆንግ ኡን በበኩላቸው፤ ፑቲን ለሰሜን ኮሪያ ወታደሮች ስለሰጡት እውቅና አመስግነው፤ በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለው ግንኙነት እየጠነከረ መምጣቱን ገልፀዋል።
እንዲሁም "ለሩሲያ ማድረግ የምችለው ወይም ማድረግ ያለብኝ ነገር ካለ እንደ ወንድማማችነት ግዴታ አድርጌ እቆጥረዋለሁ” ሲሉ ኪም ለፑቲን ተናግረዋል።
ከጦርነቱ ባሻገር ኪም በጦርነት የተጎዳውን የኩርስክ ግዛት መልሶ ለመገንባት የሚረዱ ሰራተኞችን እንደሚልኩ ቃል ገብተዋል።
ኪም ለወደቁ የሰሜን ኮሪያ ወታደሮች ቤተሰቦች ድጋፍ እንደሚያደርጉ እና መታሰቢያ ሃውልት እንደሚያቆሙላቸው መግለፃቸውን ቢቢሲ ዘግቧል።
ሁለቱ ሀገራት ከዚህ ቀደም የውጭ ጥቃት በሚደርስበት ጊዜ የጋራ ድጋፍ ለማድረግ የሚያስችል የመከላከያ ስምምነት መፈራረማቸው ይታወሳል።
በሴራን ታደሰ
#EBC #EBCdotstream #militaryparade #Russia #NorthKorea