ግብፆች ኢትዮጵያ በዓባይ ወንዝ ላይ ምንም ልማት ላታከናውን ቃል ገብታለች በሚል የተሳሳተ ሃሳብ ሲያዘዋውሩ የነበረ ቢሆንም ኡስታዝ ጀማል በሽር ግን ይህ ሃሳብ ሃሰት መሆኑን በበርካታ ሚዲያዎች ላይ በማስረዳት እውነታውን አሳውቀዋል።
ታዲያ በቁጭት የተጀመረው የግድቡን ዕውነታ ማሳወቅን መሠረት ያደረገው ኪንግስ ኦፍ ዓባይ የዩቱዩብ ገፅ እና ኡስታዝ ጀማል በሽር የተሰኘው ይፋዊ የፌስ ቡክ ገፅ ላይ መረጃዎችን ለዓለም አቀፉ ማኀበረሰብ በማጋራት የተሳሳቱ መረጃዎችን ቀልብሰዋል።
ኡስታዝ ጀማል በሽር የታላቁን ሕዳሴ ግድብ ዕውነታ ለዓለም አቀፉ ማኀበረሰብ ለማስረዳት በማኀበራዊ ትስስር ገፆች ባደረጉት ትግል በበርካቶች ዘንድ ይታወቃሉ።
በቀን ከ40 ደቂቃ ጀምሮ እስከ 10 ሰዓት የሚዘልቁ የቀጥታ ስርጭቶችን በማድረግ ከ50 ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑ ተመልካቾች እውነታውን አጋርተዋል።
ግብፆች በዓባይ ላይ የበላይ ሆነው በብቸኝነት ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ የሄዱበት ርቀት አፍሪካን የበደለ እና የከፋፈለ ነበር ይላሉ ኡስታዝ ጀማል።
ለዓለም አቀፉ ማኀበረሰብ ስለግድቡ እውነታውን የማሳወቅ ሥራ አሁንም መቀጠል አለበት ይላሉ።
በተለይ የአረቡ ዓለም ሕዳሴ ለታችኞቹ የተፋሰስ ሀገራት እና ለቀጣናው ያለውን ጥቅም እንዲረዳ በማድረግ የተጠናከረ የኮሙኒኬሽን ሥራ እንደሚያስፈልግም ያስረዳሉ።
በሄለን ተስፋዬ