ዩክሬን የሩሲያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን ከዩክሬኑ ፕሬዚዳንት ቮሎዲሚር ዘለንስኪ ጋር በሞስኮ ለመገናኘት ያቀረቡትን ሀሳብ ውድቅ አድርጋለች።
ዘለንስኪ የሰላም ድርድር ለማድረግ ወደ ሞስኮ መምጣት እንደሚችሉ ቭላድሚር ፑቲን በቤጂንግ ለጋዜጠኞች ገልጸው ነበር።
ስብሰባው በጥሩ ሁኔታ ከተዘጋጀ እና አዎንታዊ ውጤት ካስገኘ ብቻ እንደሚካሄድም በወቅቱ ተናግረው ነበር።
ይሁን እንጂ የዩክሬን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንድሬይ ሲቢጋ በኤክስ ገጻቸው ላይ “በሞስኮ የሚደረግ ስብሰባ ተቀባይነት የለውም” በማለት ፑቲን “ሁሉንም ሰው የሚያበሳጩ” ሀሳቦችን እያቀረቡ ነው ሲሉ ወቅሰዋል።
አንድሬይ ሲቢጋ " በአሁኑ ወቅት ቢያንስ ሰባት ሀገራት ፑቲን እና ዘለንስኪን ለማገናኘት ዝግጁ ናቸው።ዘለንስኪም ለዚህ በማንኛውም ጊዜ ዝግጁ ናቸው፤ ሆኖም ግን ፑቲን ሆን ብለው ተቀባይነት የሌላቸው ሀሳቦችን ማንሳት ቀጥለዋል" ብለዋል።
በሰለሞን ገዳ