የደቡብ አፍሪካ ፕሬዚዳንት ሲሪል ራማፎዛ በበይነ መረብ በተካሔደው የብሪክስ አስቸኳይ መሪዎች ስብሰባ ላይ በዓለም አቀፍ የንግድ ጉዳዮች ላይ የቡድኑን አንድነት ለማጠናከር ጥሪ አቅርበዋል ።
ፕሬዚዳንቱ፣ በአሁኑ ወቅት ዓለም “የብጥብጥና የትርምስ” ዘመን ውስጥ በመሆኗ የታዳጊ ሀገራትን የልማት ጉዞ አደጋ ላይ እንደጣለ አስጠንቅቀዋል።
በንግግራቸው፣ የዓለም ኢኮኖሚ ከነጠላ የበላይነት ወደ ብዙ የበላይነት እየተሸጋገረ መሆኑን ገልጸው፣ ይህ ሽግግር በከፍተኛ የጂኦፖለቲካዊ ውጥረት፣ የንግድ ጦርነቶች እና የጥበቃ ፖሊሲ (protectionism) መመለስ የታጀበ መሆኑን አመልክተዋል። ፕሬዚዳንቱ እነዚህ አዝማሚያዎች በማደግ ላይ ባሉ ሀገራት ላይ ከፍተኛ ጉዳት እያደረሱ መሆኑንም አጽንዖት ሰጥተዋል።
“አዲሱ የንግድ ሥርዓት የፈጠረው እርግጠኛ አለመሆን በራሴ ሀገር በደቡብ አፍሪካ ውስጥ ባለው የቅጥር ሁኔታ ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ አሳድሯል” ያሉት ፕሬዚዳንት ራማፎዛ፣ ይህ ሁኔታ ለኢኮኖሚያችን ዕድገት እንቅፋት ነው ሲሉ አስረድተዋል።
ራማፎዛ፣ አንድ ወገን ብቻ የሚወስነው የታሪፍ እርምጃ (unilateral tariff) እና እየተከፋፈለ የመጣው ዓለም አቀፍ የንግድ ሥርዓት፣ የታዳጊ ሀገራትን የወደፊት ዕድል እንደሚያናጋ አስጠንቅቀዋል።
የብሪክስ አባል ሀገራትም በጋራ በመሆን በብዙኃን ትብብርና በትርጉም ባለው ትብብር ላይ የተመሰረተ ይበልጥ ፍትሐዊና ጠንካራ የዓለም ሥርዓት ለመቅረጽ የፊት አውራሪ መሆን እንዳለባቸው ጥሪ አቅርበዋል።
ፕሬዚዳንቱ፣ የታዳጊ ሀገራት ከዓለም አቀፍ የዕሴት ሰንሰለት (global value chains) ዝቅተኛ ደረጃ እንዲወጡ ለማድረግ የዓለም ንግድ ድርጅት (WTO) እና ሌሎች የብዙኃን ሥርዓቶችን ለማሻሻል አጥብቀው አሳስበዋል። “ዓለም አቀፍ ንግድ ለሁላችንም የሚጠቅም መሆን አለበት” ሲሉም አፅንዖት ሰጥተዋል።
የአፍሪካን ስትራቴጂያዊ ጠቀሜታ በማጉላት፣ ፕሬዚዳንት ራማፎዛ አፍሪካን ጥሬ ዕቃ አቅራቢ ብቻ ሳይሆን፣ ለአዳዲስ ፈጠራ፣ ለዕሴት ፈጠራ እና ለቀጠናዊ ውህደት የዓለም አቀፍ የኢኮኖሚ ማዕከል እንድትሆን የሚያስችል ራዕይ አካፍለዋል። ይህም “ራዕያችን አፍሪካ የዓለም አቀፍ ንግድ የልብ ምት እንድትሆን ነው” ብለዋል።
በአሁኑ ወቅት የቡድን-20 ሊቀመንበር የሆነችው ደቡብ አፍሪካ፣ በኦኮኖሚክስ የኖቤል ሽልማት አሸናፊው ፕሮፌሰር ጆሴፍ ስቲግሊትዝ የሚመራ የዓለም አቀፍ የሀብት አለመመጣጠን ገለልተኛ ባለሙያዎች ኮሚቴ ማቋቋሟን ተናግረዋል።
ይህ ኮሚቴ የመጀመሪያውን ዓለም አቀፍ የፍትሃዊነት ሪፖርት ለጂ-20 መሪዎች ያቀርባል ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን፣ ይህም ድህነትን፣ ኢ-ፍትሃዊነትን እና የልማት አለመመጣጠንን ለመፍታት የሚያስችሉ መፍትሄዎችን ያቀርባል።
በዓለም አቀፍ ደህንነት ጉዳይ ላይ ደግሞ፣ ራማፎዛ በፍልስጤም በጋዛ የሚደረገው ጥቃት እንዲቆም ብራዚል ያቀረበችውን ጥሪ በመደገፍ፣ ሰላምና ልማት እርስ በእርስ የሚደጋገፉ ግቦች መሆናቸውን ግለጸዋል።
በመጨረሻም፣ የብሪክስ ኢኮኖሚ አጋርነት ስትራቴጂ 2030 እንዲጠናቀቅ ጥሪ ያቀረቡት ራማፎዛ፣ አባል ሀገራት ከ"ችግር ማብረጃ (firefighting)" ሁናቴ ወደ ስትራቴጂያዊ እርምጃ እንዲሸጋገሩ አሳስበዋል።
በአሁኑ ወቅት የዓለም ኢኮኖሚ መከፋፈል እየተባባሰ በመጣበት በዚህ ወቅት፣ የራማፎዛ ንግግር ብሪክስ ለዓለም መረጋጋትና ማሻሻያ ማሳያ ምሰሶ ሊሆን እንደሚችል የሚያሳይ ነው።
“ይህ የዓለም የንግድ ቀውስ ነገሮችን በተለየ መንገድ ለማድረግ ትልቅ ዕድል ይሰጠናል” በማለት “በአጋርነትና በአንድነት መንፈስ እነዚህን ሁሉ አስፈላጊ እርምጃዎች በጋራ እንዲወሰዱ ማስገንዘባቸውን ሩሲያ ቱዴይ ዘግቧል።
በሰለሞን ገዳ