ሬዲዮ ለሁሉም ቤተኛ የሆነ ተመራጭ እና ተደራሽ የመረጃ ምንጭ ነው፡፡
ለመሆኑ ይህ የሁሉም ቤተኛ የሆነው ሬዲዮ እንዴት ተጀመረ?
ሬዲዮ ዛሬ ለደረሰበት የዘመናዊ የዕድገት ደረጃ ብዙ ዓመታትን ፈጅቷል፤ የበርካታ ተመራማሪዎችን ጥረትንም ጠይቋል፡፡
እንደነ ቶማስ ኤዲሰን፣ ኒኮላ ቴስላ እና ጎግሊ ኢልሞ ማርኮን የመሳሰሉ የፈጠራ እና የምርምር ጠቢባን ጊዜ እና እውቀታቸውን ለግሰዋል፡፡
እ.አ.አ በ1877 ዓ.ም ኒኮላ ቴስላ መልዕክት እንዴት ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ ያለ ሽቦ እንደሚተላለፍ በምርምር ደረሰበት፤ ይህንኑ ተከትሎ ሌሎች ተመራማሪዎች በቀደመው ግኝት ላይ በመመርኮዝ ቴክኖሎጂውን ለማሻሻል ሞከሩ፡፡
ማርኮኒ እ.አ.ኤ በ1879 ዓ.ም ከቴስላ የተሻለ እና በገመድ አልባ ቴሌግራፍ አማካኝነት መልዕክትን ከአንድ ቦታ ወደሌላ ቦታ በሞገድ ኃይል ማስተላለፍ እንደሚቻል በተግባር አረጋገጠ፡፡
ማርኮኒ ራድዮ ሞገድን በመጠቀም መልዕክትን በመሬት፣ በአየር፣ በውኃ እና በሕዋ ላይ 2ኪ.ሜ ብቻ ይጓዝ የነበረውን የሬዲዮ ሞገድ በማሻሻል፣ ከ1 ሺህ እስከ 10 ሺህ ኪ.ሜ መጓዝ እንዲችል የሚያግዝ ቴክኖሎጂ በማስተዋወቁ ዓለም ቆሞ አጨበጨበለት፡፡
የሬዲዮ ታሪክ ሲነሳ ስሙ ጎልቶ የሚነሳው ማርኮኒ በ20 ዓመቱ በሬዲዮ ሞገድ ዙሪያ ምርምር ማድረግ መጀመሩ ይነገርለታል፡፡
ሕልሙ ተሳክቶለት የሬዲዮ ሞገድን በረጅም ርቀት መጓዝ የሚችልበትን የገመድ አልባ የቴሌግራፍ ቴክኖሎጂ አበልፅጎ ለፈጠራ ስራው የባለቤትነት መብት 1889 ያቀረበው ጥያቄ በዓመቱ በ1890 ፀድቆለታል፡፡
የባለቤትነት መብቱን ካረጋገጠ በኋላ በምርምሩ ገፍቶበት በገመድ አልባ የቴሌግራፍ ዘርፍ 800 የሚደርሱ የባለቤትነት መብቶችን ማግኘቱም ይጠቀሳል፡፡
50 ሺህ ፓውንድ በማውጣት በገነባው የሬዲዮ ስርጭት ማስተላለፊያ ጣቢያ አማካኝነት ሬዲዮ በአትላንቲክ ውቅያኖስ ላይ መልዕክት ማስተላፍ እና መቀበል እንደሚችልም በተግባር በማሳየቱ፣ ግንኙነት መስመራቸው እጅግ ውስን እና ኋላ ቀር የነበሩት መርከቦችም በሬዲዮ መገናኘት በመጀመራቸው እፎይታን አገኙ፡፡
መርከቦች ለአደጋ ሲጋለጡ በሬዲዮ አማካኝነት መልዕክት መለዋወጥ በመቻሉ፣ የአደጋ ጊዜ ሰራተኞች በፍጥነት ወደ ስፍራው በመምጣት እርዳታ እንዲሰጡ አግዟል፡፡
ለዚህም በትልቁ በምሳሌነት የምትነሳው ግዙፏ ታይታኒክ መርከብ ናት፡፡
የታይታኒክ መርከብ ከበረዶ ግግር ጋር ተላትማ ተሰባብራ ስትሰምጥ የ700 ሰዎችን ሕይወት ማትረፍ የተቻለው በቴሌግራፍ በተላለፈ መልዕክት አማካኝነት ነው፡፡
በዚህም ማርኮኒ ላበረከተው አስተዋፅኦ የወርቅ ሜዳሊያ የተሸለመ ሲሆን ለአበርክቶውም አቻ የለውም በማለት ተሞካሽቷል፡፡
የሬዲዮ አባት በመባል የሚጠራው ጎግሊ ኢልሞ ማርኮኒ በ63 ዓመቱ ከዚህ ዓለም በሞት በተለየበት ወቅት፣ በዓለም ላይ የሚገኙ ሬዲዮ ጣቢያዎች በሙሉ ለ2 ደቂቃ ያሕል ስርጭታቸውን በማቋረጥ ለራዲዮ ፈጣሪው ማርኮኒ ያላቸውን ክብር አሳይተዋል፡፡
የጀርመኑን ዶቼቬሌን በ20 ዓመት፣ የአሜሪካውን የአማርኛ ድምፅ ቪኦኤን በ6 ዓመት የሚበልጠው የኢትዮጵያውያን የበኩር ድምፅ የሆነው የኢትዮጵያ ሬዲዮ ተደራሽነቱን እያሰፋ ለ90 ዓመታት ዘልቋል፡፡
በንፍታሌም እንግዳ ወርቅ