ታላቁ የሕዳሴ ግድብ በኢትዮጵያውያን የጋራ ርብርብ እና ፅናት እውን መሆን ችሏል ሲሉ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የውኃ ምህንድስና ተባባሪ ፕሮፌሰር የሆኑት ዘለቀ አግዴ (ዶ/ር) ገለጹ።
ዶ/ር ዘለቀ ከኢቲቪ ጋር በነበራቸው ቆይታ፥ ኢትዮጵያውያን በከፍተኛ የውጭ ጫና ውስጥ አልፈው በራስ አቅም ግድቡን ገንብተው ለምረቃው መብቃታቸው ትልቅ ድል ነው ብለዋል።
በተለያዩ ጊዜያት ተስፋ አስቆራጭ የሚመስሉ መሰናክሎች አጋጥመው የነበረ ቢሆንም፤ የኢትዮጵያ መንግሥት እና ህዝብ በወሰዱት ቁርጠኛ አቋም ግድቡ ትልቅ መስዋዕትነት ተከፍሎበት ለስኬት መብቃቱን ገልጸዋል።
በፍትሃዊ የጋራ ተጠቃሚነት መርሆዋ ላይ ፀንታ ሌሎች የተፋሰሱን ሀገራት በማስተባበር በትውልድ ቅብብሎሽ ለዘመናት ስትታገል የቆየችው ኢትዮጵያ በመጨረሻ ጣፋጩን ድል ማጣጣም ችላለች ብለዋል።
በታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ፕሮጀክት የተገኘው ስኬት የተፋሰሱን ሀገራት ጨምሮ በመላ አፍሪካውያን ዘንድ መነሳሳትን የሚፈጥር መሆኑን ገልጸው፤ የዚህ ትውልድ አባል በመሆናችን ታሪክ ሲያወሳን እና ሲያወድሰን ይኖራል ብለዋል።
በሜሮን ንብረት
#Ethiopia #GERD #Inauguration