ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ይህን ያሉት ከዚህ ቀደም በኢትዮጵያ የባሕር በር ጥያቄ ዙሪያ ማብራሪያ በሰጡበት ወቅት ነበር።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማብራሪያቸው፥ ኢትዮጵያ ያላትን ሀብት እያካፈለች፣ የእኛን አትንኩ፣ የእናንተን ብቻ ስጡን ማለት ትክክል አይደለም ሲሉ ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ ተከዜን ለኤርትራ፤ ዓባይን ለሱዳን እና ለግብፅ፤ ባሮን ለደቡብ ሱዳን፤ ኦሞን ለኬንያ፤ ገናሌ፣ ዳዋ እና ዋቢ ሸበሌን ለሶማሊያ የውሃ ሀብቷን ያለ ስስት እንደምትሰጥ ዘርዝረዋል።
ከኢትዮጵያ ጎረቤቶች መካከል ከኢትዮጵያ የወንዝ ውሃ የማይፈስስላት ጅቡቲም ውሃ ማግኘት አለባት በሚል ቧንቧ ተዘርግቶ ተሰጥቷታል ብለዋል።
ጎረቤት ሀገራቱ ለኢትዮጵያ ምንም ውሃ የማይሰጡ ሁሉም ተቀባይ መሆናቸውን ጠቅሰው፤ ታዲያ ወንዞቿን ያለ ስስት ወደ ጎረቤቶቿ የምታፈስስ ሀገር ቀይ ባሕርን መጠየቋ ለምን ነውር ይሆናል ሲሉ አግራሞታቸውን ገልጸዋል።
የእናንተን ብቻ እንካፈል፣ የእኛን እንዳትጠይቁን ማለት ስህተት መሆኑንም አመላክተዋል።
የኢትዮጵያ ጥያቄ በታሪክ ላይ የተመሰረተ መሆኑን አንስተው፤ ለማሳያ በአንድ ወቅት ራስ አሉላ አባነጋ "ራሱ ቀይ ባሕር የኢትዮጰያ የተፈጥሮ ወሰን ሆኖ ኖሯል፣ ይኖራልም” ስለማለታቸው ጠቅሰዋል።
ኢትዮጵያ መብቷን በኃይል የማስከበር የማስከበር ፍላጎት እንደሌላት በመግለጽም ችግሮቻችንን በዲፕሎማሲ በመፍታት በጋራ እንደግ ሲሉ ጥሪ አቅርበዋል።
በቢታንያ ሲሳይ
#ebcdotstream #ethiopia #redsea