የኢትዮጵያ አካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ለሊሴ ነሜ፥ ባለፉት 7 ዓመታት በተተገበረው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብር ብክለትን ከመግታት አኳያ ብዙ ፋይዳ መገኘቱን ተናግረዋል።
ዋና ዳይሬክተሯ ለኢቲቪ 57 የዜና መሰናዶ እንዳሉት፥ የችግኝ ተከላ መርሐ ግብሩ የአየር ብክለት እንዲቀንስ ፣ የተራቆቱ መሬቶች እንዲያገግሙ ፣ በአፈር እና በውኃ ላይ የሚከሰቱ ብክለቶች እንዲጠበቁ ማድረግ እንዳስቻለም አንስተዋል።
የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብር ለትውልድ ንፁህ እና ነፋሻማ ኢትዮጵያን እንድናስተላልፍ ትልቁን ድርሻ ይይዛልም ነው ያሉት።
የኢትዮጵያ አካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን የአካባቢ ብክለትን ለመግታት ሁሉም ኢትዮጵያዊ እንዲተባበር፤ ለማህበረሰቡ ግንዛቤ የማስጨበጥ ሥራ እየሰራን ነውም ብለዋል።
የዘንድሮው የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ከተጀመረ አንድ ወር ያስቆጠረ ሲሆን፤ ባህል ሆኖ እንዲቀጥል ሁላችንም የራሳችንን ኃላፊነት ልንወጣ ይገባልም ብለዋል ዋና ዳይሬክተሯ።
በሀ/ሚካኤል ክፍሉ