ይህ 2.9 ኪ.ሜትር ርዝመት ያለው የምድር ውስጥ ባቡር መስመር ፕሮጀክት በበርካታ የፖለቲካ ትርምሶች የኢኮኖሚ ውድቀቶች እና በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ውስጥ አልፏል። እንዲህም ሆኖ ታዲያ ዛሬ በታቀደ በ92ኛ ዓመቱ የተጠናቀቀ የኒውዮርክን የማያቋርጥ የዕድገት ፍላጎት የሚያሳይ አስገራሚ የምህንድስና ታሪክ ያለው ፕሮጀክት ነው።
በ1920ዎቹ መጨረሻ በይፋ የታቀደው ይህ የኒውዮርክ ሁለተኛ አቬኑ የምድር ውስጥ ባቡር መስመር ግንባታ ከፕሬዝዳንት ዋረን ጂ. ሃርዲንግ ዘመን ጀምሮ አስከ ፕሬዝዳንት ኦባማ የአስተዳደር ዘመን ድረስ የዘለቀ የትውልድ ቅብብሎሽን የሚያሳይ ታሪክ ነው።
በወቅቱ አሜሪካንን ይመሩ በነበሩት በፕሬዝደንት ዋረን ጂ. ሀርዲንግ የስልጣን ዘመን የታቀደው ይህ ፕሮጀክት ከሳቸው በኋላም በነበሩት ፕሬዝደንቶች በተለያዩ ችግሮች ምክንያት ሳይጀመር ቆይቷል።
ከዛ በኋላም በፕሬዝዳንት ፍራንከሊን ዲ. ሩዝቬልት ዘመን በተካሄደው የሁለተኛው የአለም ጦርነት ምክንያትና ጦርነቱን ተከትሎ በተከሰተው የሀብት አጥረት ሳይጀመር ቀርቷል። በእርግጥ ይህ ብቻ አልነበረም ምክንያቱ በፕሬዝዳንት አይዘንሃወር እና ትሩማን ዘመን ትኩረት የተደረገው ዋና ዋና አውራ ጎዳናዎችን በመገንባት ላይ በመሆኑ ይህ የምድር ውስጥ ባቡር መስመር ስራው ሳይጀመር እንዲቆይ ምክንያት ሆኗል።
ከእነዚህ ፕሬዝደንቶች ቀጥሎ ወደ ስልጣን በመጡት መሪዎች ዘመንም የአሜሪካ ኢኮኖሚ እየተሻሻለ ቢመጣም ይህንን ግዙፍ ፕሮጀክት ለማስጀመር የሚያስችል ሁኔታ ሳይፈጠር ቆየ። በጥቂት አመታት ተጠናቆ ስራው ይጀመራል የተባለለት የሁለተኛው አቬኑ የባቡር መስመር ግንባታን ለመጀመር ያልፈለገ መሪ አልነበረም ግን አስቻይ ጉዳዮች ሳይኖሩ በመቅረታቸው በዚህ ፕሮጀክት ምክንያት የልቡ የሞላለት መሪ መሻቱ የተሳካላት አመራር ሳይኖር ቀረ።
በመጨረሻ ግን በ1972 በፕሬዝዳንት ሪቻርድ ኒክሰን የስልጣን ዘመን ትኩረትም አግኝቶ ጊዜውም ሆኖ ግንባታውን ለመጀመር የሚያስችል የገንዘብ ድጋፍ በመገኘቱ ስራው ተጀመረ።
በዚህ እለት የታተመው የኒውዮርክ ታይምስ ጋዜጣም በፊት ገፁ ላይ ለመገንባት ከታቀደ ከ52 ዓመታት በኋላ ስራው ስለተጀመረው የሁለተኛው አቬኑ የባቡር መስመር ግንባታ ስራ መጀመሩን የሚያበስር ይዘት ያለው ሀተታ ይዞ ሲወጣ እንዲህ የሚል ነበር፦
"የኒውዮርክ ከተማ ከ1920ዎቹ ጀምሮ ለመገንባት ስትታገልበት የኖረችው በምስራቅ ማንሃታን ላይ የነበረውን የትራንስፖርት ቀውስ ለመፍታት ያግዛል የተባለውን የምድር ውስጥ ባቡር መስመር ፕሮጀክት በከተማዋ ገዥ ኔልሰን ኤ. ሮክፌለር እና በኒውዮርክ ከንቲባ ጆን ቪ. ሲንሳይ የመሰረት ድንጋዩ ተጥሎ ስራው ተጀመረ" የሚል ረጅም ዘገባ በፊት ገጽ ይዞ ነው የወጣ።
በወቅቱ በዓለም ላይ አጅግ በጣም ከተጨናነቁ የባቡር መስመሮች መሀከል አንዱ የነበረውን የኒውዮርክ ከተማ የትራፊክ መጨናነቅ ለማስወገድ መፍትሄ እንደሚሆን ታምኖበት ስራው የተጀመረው ይህ የሁለተኛው ጎዳና የመሬት ውስጥ ባቡር መስመር አቅዱ የወጣው በ1920ዎቹ ነበር።
ይህ ወቅት አሜሪካ በከፍተኛ የኢኮኖሚ አለመረጋጋት ውስጥ የነበረችበት ጊዜ በመሆኑ ይህ ፕሮጀክት ወደ ስራ ሳይገባ አመታት ማለፍ ጀመሩ።
የኒውዮርክ ማንሃታን የትራንስፖርት ችግርም ግማሽ ዘመናትን ተሻግሮ 52 አመታት ተቆጠሩ፡፡ እንግዲህ ከዚህ በኋላ ነው የአሜሪካን ኢኮኖሚ ጠንክሮ ይህን ፕሮጀክት ለመገንባት ዝግጁ መሆኑ ሲታወቅ ከግማሽ ከፍለ ዘመን በላይ ያስቆጠረው የሁለተኛው ጎዳና የባቡር መስመር የግንባታ አቅድ አቧራውን አራግፎ በተግባር ላይ ሊውል የመሰረት ድንጋይ ተጥሎ ስራው የተጀመረው።
ስራው ከተጀመረ በኋላም መሐንዲሶች በሁለተኛ አቬኑ ጎዳና ስር የሚገኘውን የውስጥ ለውስጥ መስመር እየቆፈሩ ረጅም የዋሻ መንገድ ተሰራ።
በዚህ መልኩ ስራው እየተከናወነ እያለ ግን አሜሪካን በ1970ዎቹ አጋማሽ ላይ ባጋጠማት የኢኮኖሚ ውድቀት ምክንያት ግንባታው ሙሉ በሙሉ ቆመ።
እነዚህ በ1970ዎቹ የተቆፈሩት ዋሻዎች በፕሬዝደንት ጂሚ ካርተር፣ ሮናልድ ሬገን፣ በደብልዩ ቡሽ አና በፕሬዝደንት ቢል ክሊንተን ዘመን ግንባታቸው ሳይጀመር ለ32 ዓመታት ያህል ተዘግተው ቆዩ።
በዚህ ወቅት ነው ያላንዳች እንቅስቃሴ ተቆፍረው የተተውት የምድር ውስጥ የባቡር መስመሮች "የመናፍስት ዋሻ“ የሚል ቅፅል ስም የተሰጣቸው።
በዚህ ላይ እያለም በየጊዜው እየጨመረ የመጣውን የህዝብ ብዛት ማስተናገድ የተሳነውን የትራንስፖርት መሰረተ ልማት ለማቃለል እንዲያስችል ስራው ተጀምሮ ለ32 አመታት ተዘግቶ የቆየው የሁለተኛው ጎዳና የምድር ውስጥ ባቡር ግንባታ በፕሬዝዳንት ጆርጅ ደብልዩ ቡሽ አስተዳደር ዘመን በ2007 ዓ.ም ተነቃቅቶ አንደገና ስራው ተጀመረ።

አቅዱ ከወጣ በኋላ በአቅም ውሱንነት ምክንያት ለ52 አመታት ሳይጀመር የቆየው ከተጀመረም በኋላ በተለያዩ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች ሲቆም እንደገና ሲጀመር አመታትን ያስቆጠረው ይህ ፕሮጀክት በ2007 ስራው ከተጀመረ በኋላ መሻሻል ያለባቸውን ዲዛይኖች በማሻሻልና በዓለም ትልቁን የዋሻ መቆፈሪያ ማሽን በስራ ላይ በማዋል ለውጤት ሰማብቃት ቀን ከሌት መስራት ተጀመረ።
4.4 ቢሊየን የአሜሪካን ዶላር በጀት ተመድቦለት ዘመናዊነትን ባካተተ መልኩ እየተሻሻለ ስራው የቀጠለው ይህ የኒውዮርክ ማንሀታን የምድር ውስጥ ባቡር መስመር በከፍተኛ ወጭ እና የረቀቁ የግንባታ መሳሪያዎች በመታገዝ ከፕሬዝደንት ጆርጅ ቡሽ በኋላ ለስምንት አመታት አሜሪካንን በመሯት በፕሬዝደንት ባራክ አባማ ዘመነ መንግስትም ቀጥሎ 96ኛ፣ 86ኛ እና 72ኛ የተባሉት የባቡር መስመሮች ከአስር አመታት ያልተቋረጠ ግንባታ በኋላ በጥር ወር 2017 ተጠናቅቀው ለአገልግሎት ከፍት ሆኑ።

እጅግ ባማረ እና ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችን በውስጡ በማካተት የተሰራው ፕሮጀክት በአጭር መስመር ከፍተኛ ወጭ የወጣበት የአለማችን ውድ የዋሻ ውስጥ መንገድ መሆን ቻለ።
ይህ ለአመታት የዘለቀው የኒውዮርክ የምድር ውሰጥ ባቡር ጣቢያ ፕሮጀክት አሁንም አልቆመም እስከ ሀርለም ጫፍ የሚደርሰውን ሁለተኛውን ፕሮጀክት ለመጀመር የሚያስፈልገው በጀት ፀድቆ ስራውን ለመጀመር ጥናቶች እየተካሄዱ ይገኛሉ።
መደምደሚያ፦
የሁለተኛ አቬኑ የምድር ውስጥ ባቡር ፕሮጀክት ትርጉሙ ከቀላል የትራንስፖርት መስመር በላይ የሆነና ለ98 ዓመታት የዘለቀ የማያቋርጥ የጽናት መታሰቢያ ተደርጎ የሚወሰድ ነው።
አቅዱ ሳይተገበር ለአምሳ ሁለት አመት የቆየው በ1970ዎቹ ስራው ተጀምሮ ዋሻዎች ከተቆፈሩ በኋላ ለ32 ዓመታት ተረስተው በመቆየታቸው "የመናፍስት ዋሻዎች“ እስከመባል የደረሰው በመጨረሻም በአለም ውድ የተባለ በጀት ተመድቦለት የተጠናቀቀው ይህ ፕሮጀክት ከትውልድ ትውልድ የዘለቀ በብዙ ተግዳሮቶች አልፎ ለውጤት መብቃት የቻለ የመልማት ፍላጎት ተምሳሌትም ነው።
በውስጡ ሙዚየሞችን አካቶ የተገነባው እጅግ ዘመናዊ የምድር ውስጥ የባቡር መስመር ግንባታ ምንም እንኳን የመጀመሪያው ምዕራፍ ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት ቢጀምርም በቀጣይ ወደ ሰሜን ሃርሰም አና ደቡብ ወደ ፊናንስ ዲስትሪክት ለማራዘም አቅድ ተይዞ ይህንን ቀጣይ ፕሮጀክት ለመገንባት ጥናቶች እየተካሄዱ ይገኛል።
በዓለም ላይ ታላላቅ ህልሞች በአንድ ሰው ወይም በአንድ ትውልድ ሊታሰቡ ወይም ሊጀመሩ ይችላሉ። ሂደቱን እና ማጠናቀቁን የሚረከብ አስተዋይ እና ከዋናው ዓላማ የማይዛነፍ ትውልድን ግን የሚጠይቅ ነው። ለዚህም ነው እንዲህ ያሉ ፕሮጀክቶች በብዙ ትውልዶች ተስፋና በብዙ መሪዎች የማይናውጽ አቋም ህያው ሆነው የምናየው።
ዛሬ ይህ ፕሮጀክት ተጠናቆ የሚመላለሱበት ሰዎች ስለዘመናዊነቱ እና ስለባቡሮቹ ፍጥነት ወይም አገልግሎት ተገርመው ሲያወሩ አሊያም ሲጽፉ ሊሰሙ ይችላሉ። ይህ ግን ዛሪ ኒውዮርክን ለረገጠ የዓለም ሰው ሁሉ ምቹ አገልግሎት የሚሰጠው የምድር ውስጥ የባቡር መንገድ እንዴት እንደታሰበ እና ዘመናትን በብዙ ውጣውረድ ማለፉን የሚያውቁ ጥቂቶች ብቻ ናቸው። አንድ እውነት ግን አለ ዓላሚ፣ ገፈት ቀማሽ እና ፈጻሚ ትውልድ የሌለው ሀገር ቀጣይነቱ ጥያቄ ውስጥ መውደቁ አያጠያይቅም።