ቱርኪዬ በቀጣይ ዓመት የሚደረገውን 31ኛውን የአየር ንብረት ጉባኤ (COP31) እንድታዘጋጅ ተመርጣለች፡፡
ሀገሪቱ ጉባኤውን በሜዲትራንያን የሪዞርት ከተማ በሆነችው አንታሊያ ከተማ እንደምታስተናግድም ተገልጿል፡፡
ጉባኤውን ለማስተናገድ ከቱርኪዬ ጋር ከፍተኛ ፉክክር ውስጥ የነበረቸው አውስትራሊያ የቅድመ ጉባኤ የሀገራት መሪዎችን ድርድር እንድታስተናግድ ሚና ተሰጥቷል፡፡
ቱርኪዬ እና አውስትራሊያ በቀጣይ ዓመት የሚዘጋጀውን ጉባኤ ወደ ሀገራቸው ለመውሰድ ከፍተኛ ፉክክር ውስጥ ገብተው የነበረ ሲሆን፣ በመጨረሻ ባደረጉት ስምምነት ቱርኪዬ ዋናውን ጉባኤ እንድታዘጋጅ እና አውስትራሊያ የመሪዎችን ውይይት እንድትመራ ተወስኗል።
አውስትራሊያ በቅድመ ጉባኤው የሚደረገውን የመሪዎች የድርድር መድረክ አዘጋጅ እና የፓስፊክ ቀጣና የድርድር ፕሬዝዳንት ሆና መመረጧን ነው የአውስትራሊያው ጠቅላይ ሚኒስትር አንቶኒ አልባኒዝ ያስታወቁት።
በውጤቱ ደስተኛ እንዳልሆኑ የገለጹት የፓፑዋ ኒው ጊኒ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጀስቲን ትካቼንኮ በበኩላቸው፤ የፓስፊክ ቀጣና ሀገራት ሙሉ ዝግጅቱን መውሰድ ይገባቸው ነበር ብለዋል።
ጉባኤውን በአንታሊያ ከተማ እንደምታስተናግደው የገለጸችው ቱርኪዬ፤ ዕድሉን ተጠቅማ በታዳጊ እና በበለፀጉ ሀገራት መካከል ያለውን ግንኙነት ለማሻሻል እንደምትሠራ አስታውቃለች።
በለሚ ታደሰ
#EBC #EBCdotstream #Türkiye #ClimateAction #COP30 #COP31 #COP32