የብሔራዊ ዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ምክር ቤት በዛሬው ዕለት 5ኛ መደበኛ ስብሰባውን አካሂዷል።
ምክር ቤቱ በስብሰባው በ4ኛ መደበኛ ስብሰባው እንዲፈፀሙ ያስቀመጣቸውን ተግባራት አፈፃፀም በጥልቀት በመገምግሞ አቅጣጫ አስቀምጧል።
ምክር ቤቱ አጠቃላይ የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን የሥራ ክንውን፣ የዲጂታል መታወቂያ የምዝገባ ሂደት እንዲሁም ‘የ5 ሚሊዮን የኢትዮጵያ ኮደርስ’ ኢኒሼቲቭ ትግበራ አፈጻጸምንም ገምግሞ በቀጣይ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ከስምምነት ላይ ደርሷል።

ከዚህም በተጨማሪ በኢትዮጵያ በመከናወን ላይ የሚገኙ እንዲሁም አዳዲስ የዲጂታል ሥራዎች ከዲጂታል ኢትዮጵያ ስትራቴጂ ጋር ያላቸው ተጣጣሚነት በውይይቱ ተዳሷል።
በመጨረሻም ምክር ቤቱ ረቂቅ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ላይ ጥልቅ ውይይት ካደረገ በኋላ፤ ስትራቴጂ ሰነዱን በማፅደቅ ወደ ሚኒስትሮች ምክር ቤት እንዲላክ መወሰኑን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ አስታውቀዋል።
የዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታችን በእመርታ የሚያድግበት ዘመን ላይ እንደመሆኑ፤ ምክር ቤቱም ለዚሁ ዕድገት ተገቢውን ሚና ለመወጣት የጀመረውን ጥረት አጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማኅበራዊ ትስስር ገፃቸው ባጋሩት መልዕክት።