ኢትዮጵያ ዛሬ የውበት ብቻ ሳይሆን የሥራ፣ የተስፋ ብቻ ሳይሆን የተጨባጭ ውጤት ምድር እየሆነች ነው።
በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከሀሳብ ዘር እስከ ውጤት በሚመነዘር የቃል ጉልበት የተጀመሩት የ“ገበታ ” ፕሮጀክቶች፣ ሀገራችን ለዘመናት የኖረባትን “የቀለም የዕይታ፣ የመግለጥ ድህነት” ሰብረው፣ ድብቅ ፀጋዎቻችንን ለዓለም ገበያ እያወጡ ይገኛሉ።
ከ“ገበታ ለሀገር” እስከ “ገበታ ለትውልድ”፦ የጉዞው ስኬት
የመጀመሪያው ምዕራፍ በነበረው “ገበታ ለሸገር” የተጀመረው መዲናዋን የመቀየር ተምሳሌታዊ ጉዞ ፍጥነቱን በመቀየር አድማሱን በማስፋት “ገበታ ለሀገር” ፕሮጀክቶች እንደ ጎርጎራ፣ ወንጪ እና ኮይሻ ያሉ ታላላቅ መዳረሻዎች የኢትዮጵያን አዲስ ገፅታ መገንባት ጀመሩ።
ይህ ስኬት ተስፋፍቶ ዛሬ “ገበታ ለትውልድ” በሚል የላቀ ደረጃ ላይ ደርሷል። እንደ ሃላላ ኬላ፣ ጨበራ ጩርጩራ - የዝሆን ዳና ሎጅ፣ ወንጪ-ደንዲ ኢኮ ሎጅ፦ ጎርጎራ እና ሸበሌ ሪዞርት የመሳሰሉት ፕሮጀክቶች ተራ የመዝናኛ ስፍራዎች አይደሉም፤ የኢኮኖሚ ጥንካሬያችን አዳዲስ ምሶሶዎች፣ የመለወጥ አቅማችን ውስጣዊ መገለጫ፣ የመደመር ትውልድ አዲስ ገፅታ ናቸው።
የመደመር እሳቤ
እነዚህ ሥራዎች በዘፈቀደ የሚከናወኑ ሳይሆኑ በመደመር እሳቤ ተቀድተው የታነጹ ናቸው። መደመር ማለት “ አቅማችንን ማወቅ፣ ያለንን አቅም ማቀናጀት፣ ለላቀ ውጤትና ከፍታ መነሣት” ነው። የመደመር መንግሥት፣ የግል ባለሀብቱ እና ሕዝቡ በአንድነት በመቆማቸው፣ በአጭር ጊዜ ውስጥ የማይታሰቡ የሚመስሉ ታላላቅ ፕሮጀክቶች እውን ሊሆኑ ችለዋል።
ይህ የእድገት ጉዞ ለዘመናት ኢትዮጵያ በቂ ትኩረት ባልተሰጠው በግብርና ላይ ብቻ የተንጠለጠለውን ኢኮኖሚዋን ወደ ብዝሐ ዘርፍ ኢኮኖሚ በማሸጋገር (Economic Diversification)፣ ዘላቂ እና የማይናወጥ መሠረት እየጣለች መሆኑን ያሳያል።
የኢትዮጵያ አዲስ ሚና በአፍሪካ
ዛሬ ኢትዮጵያ ለቀጠናው እና ለመላው አፍሪካ የለውጥ ሞተር (Change Agent) እየሆነች ነው። እነዚህ ፕሮጀክቶች “አፍሪካውያን በራሳቸው አቅምና እውቀት ታላላቅ ስራዎችን መስራት ይችላሉ” የሚል ትልቅ ተስፋን ሰጥተዋል። በታላቁ የሕዳሴ ግድብ የጀመርነው የኃይል የበላይነት፣ በ“ገበታ ለትውልድ” በቱሪዝምና በመሰረተ ልማት እየታጀበ ኢትዮጵያን የአፍሪካ የብልፅግና ተምሳሌት እያደረጋት ነው።
ለቀጣይ ትውልድ የሚኖረው ሚና
ለልጆቻችን የምናወርሰው ዕዳን ሳይሆን ሀብትን፣ ውርደትን ሳይሆን ኩራትን ነው። “ገበታ ለትውልድ” ማለት ነገ ልጆቻችን በሀገራቸው ተስፋ ቆርጠው እንዳይሰደዱ፣ ይልቁንም በሀገራቸው ፀጋ እንዲጠቀሙና የአለም እንግዶችን በክብር እንዲቀበሉ የሚያስችል የታሪክ አደራ ነው።
ኢትዮጵያ በትጋት ትገነባለች፤ በውበት ትመራለች!
#ebcdotstream #ገበታ_ለትውልድ #መደመር #ኢትዮጵያ #አፍሪካ_ተስፋ #PMAbiyAhmed #TourismEthiopia