Search

"ይህ 2026 እንጂ 1946 አይደለም፤ አፍሪካ በጸጥታው ምክር ቤት ቋሚ መቀመጫ ሊኖራት ይገባል" - አንቶኒዮ ጉቴሬዝ

ቅዳሜ የካቲት 07, 2018 91

የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ በ39ኛው የአፍሪካ ኅብረት የመሪዎች ጉባኤ ላይ ባደረጉት ንግግር፤ አፍሪካ በተመድ ውስጥ በሁሉም እንቅስቃሴዎች ቀዳሚ ተሳታፊ እንደምትሆን ገለጹ።
ዋና ጸሐፊው በንግግራቸው፤ "እስከ ሥልጣን ዘመኔ መጨረሻ ድረስ አፍሪካ በተመድ ውስጥ ያላት ሚና ከቀዳሚዎቹ ተርታ እንዲሰለፍና በሁለቱ ተቋማት መካከል ያለው አጋርነት ከምንጊዜውም በላይ እንዲጠነክር ለመስራት ቃል እገባለሁ" ብለዋል።
የአፍሪካ ኅብረት የቅኝ ግዛት ትግሎችን በጋራ ከመምራት ጀምሮ "ለአፍሪካ ችግሮች አፍሪካዊ መፍትሔ" በሚል መርህ እስከ ዛሬ የዘለቀ ተቋም መሆኑን ዋና ጸሐፊው አውስተዋል።
ይሁን እንጂ በሱዳን፣ በዲሞክራቲክ ኮንጎ እና በአንዳንድ የአፍሪካ ሀገራት የሚታየውን አለመረጋጋት ለመፍታት ኅብረቱ በትኩረት እንዲሰራ አሳስበዋል።
የአየር ንብረት ለውጥን ተጽዕኖ ለመቋቋም ሀገራት የታዳሽ ኃይል አማራጮችን እንዲጠቀሙ ኅብረቱ ማበረታታት እንዳለበትም ጠቁመዋል፡፡
"ይህ 2026 እንጂ 1946 አይደለም፤ በመሆኑም አፍሪካ በተመድ የጸጥታው ምክር ቤት ቋሚ መቀመጫ ሊኖራት ይገባል" ሲሉም አንቶኒዮ ጉቴሬዝ ንግግራቸውን አጠቃለዋል።
በሀብተሚካኤል ክፍሉ