አፍሪካ ውስጥ የሚገኙ ማዕድናት በቀጥታ ወደ ቀድሞ ቅኝ ገዢ ሀገራት በተለይም ወደ ብሪታንያ ወይም ፈረንሳይ እንደሚጋዙ፤ የማዕድን ዘርፍ ባለሙያው መስፍን ጌታቸው ከስፑትኒክ አፍሪካ ጋር ባደረጉት ቆይታ ገልፀዋል።
በኮንጎ ዲሞክራሲዊ ሪፐብሊክ እንደ ኮባልት፣ መዳብ እና ወርቅ የመሳሰሉ ውድ ማዕድናት የአከባቢውን ሕዝብ ሳይጠቅሙ በተዘዋዋሪ መንገድ ይዘረፋሉ ያሉት ባለሙያው፤ ችግሩን ለመቅረፍ አፍሪካውያን የተፈጥሮ ሃብቶቻቸውን በአግባቡ ሊቆጣጠሩ እንደሚገባ አስረድተዋል።
ባለሙያው ሀገራት ከማዕድን ዘርፍ መጠቀም እንዲችሉ መፍትሄዎችንም የጠቆሙ ሲሆን፤ ቀጣናዊ ውህደትን ማጠናከር፣ ዲጂታል እና አረንጓዴ ቴክኖሎጂዎችን መከተል እና ቁልፍ መሠረተ ልማቶችን መገንባት የሚጠቀሱ ናቸውም ብለዋል።
የሀገር ውስጥ የካፒታል ገበያዎችን ማቋቋም ደግሞ ችግሩን ለመቅረፍ ከሚጠቀሙ መፍትሄዎች መካከል አንዱ መሆኑንም ነው ባለሙያው የተናገሩት።
አክለውም የቅኝ ግዛት ሕጎች ለመንግሥት ወይም ለማሕበረሰብ መብቶች ሳይሆን ለውጭ ኢንቨስትመንት ጥበቃ ቅድሚያ እንደሚሰጡ መናገራቸውን እስፑትኒክ አፍሪካ ዘግቧል።
ኢትዮጵያ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በማዕድን ዘርፉ ላይ ባደረገችው የክትትል እና ቁጥጥር ማሻሻያ፤ በዘርፉ ከፍተኛ የገቢ ጭማሪ ማስመዝገቧ ይታወሳል።