በ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የታየው የህዝብ ተሳትፎ በኢትዮጵያ እውነተኛ ዴሞክራሲ ስር እየሰደደ መሆኑን ያሳያል ሲሉ የጂኦፖለቲካ ተመራማሪ እና ተንታኙ ዶ/ር ኤልያስ አቢሻክራ ተናግረዋል።
ዶ/ር ኤልያስ ከኢቢሲ ኤፍ ኤም አዲስ 97.1 ወቅታዊ ዝግጅት ላይ ባደረጉት ቆይታ በኢትዮጵያ ዴሞክራሲ ብርቅ የሚሆንበት ዘመን አብቅቷል ብለዋል።
ኢትዮጵያ ከቀጠናው ሀገራት የተሻለ የምርጫ ልምምድ እንዳላት በ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ በተግባር ማሳየቷን ገልፀዋል ።
ዶ/ር ኤልያስ ለመምረጥ የተመዘገቡ ከ54 ሚሊዮን በላይ ኢትዮጵያዊያን የአፍሪካውያን አይችሉም ትርክትን በመቀልበስ የዴሞክራሲ ዓድዋን መፍጠር ችለዋል ነው ያሉት።
ኢትዮጵያውያን ከምርጫው በፊት ሲሰራጩ የነበሩትን ሀሰተኛ ፕሮፓጋንዳዎች በመሻገር በምርጫ ብቻ የሚል ትርክት በመገንባት ግጭት ጠማቂዎችን አሳፍረዋል ሲሉ ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ ካላት ፀጋ እና የመልማት አቅም ጋር ዴሞክራሲ ሲደመር አፍሪካዊት ሀይል መሆኗ እንደማያጠራጥር አመላክተዋል።
የፖለቲካ ፓርቲዎች የመራጩን ሀይል በመገንዘብ ያገኙትን ውጤት በፀጋ በመቀበል ለአዲሱ መንግስት አጋዥ መሆን አለባቸው ያሉ ሲሆን ዜጎችም መረጃን ከተገቢው ተቋም ብቻ በመውሰድ ሀሰተኛ መረጃዎችን ማምከን እንደሚጠበቅባቸው ዶ/ር ኤልያስ አስገንዝበዋል ።
በቤተልሔም ገረመው