የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን ባለፉት አምስት ወራት ለ70 የመገናኛ ብዙኃን በፍቃድ እና ክትትል ዘርፍ የፍቃድ እና የብቃት ማረጋገጫ ሰርተፍኬት እንዲሁም የዕድሳት አገልግሎት መስጠቱን አስታውቋል።
ባለሥልጣኑ በአዋጅ በተሰጠው ተግባር እና ኃላፊነት መሠረት የሚዲያ ዘርፉን ዕድገት የሚመጥን ክትትል እና ድጋፍ ለማድረግ የሚያስችለውን ሁለን አቀፍ የሪፎርም ሥራዎች እያካሄደ እንደሚገኝ ነው የገለጸው።
ከዚህ ጋር በተያያዘም የሀገራችን መገናኛ ብዙኃኑን በቁጥር፣ በዓይነት እንዲሁም በተደራሽነት ዕድገት እንዲያስመዝግቡም የበኩሉን እስተዋፅኦ እያበረከተ ይገኛል።
በዚህም መሠረት ባለፉት አምስት ወራት (ከጥር - ግንቦት/ 2018 ዓ.ም) በባለሥልጣኑ የሀገር ውስጥ ፈቃድ ምዝገባ እና ብቃት ማረጋገጫ የተሰጣቸው እና ዕድሳት የተደረገላቸው የንግድ መገናኛ ብዙኃን፣ የማኅበረሰብ እና የበየነ መረብ መገናኛ ብዙኃን እንዲሁም የሚዲያ ፕሮግራም ዝግጅትን ጨምሮ 33 ናቸው።
የውጭ ሚዲያን በተመለከተ ደግሞ 16 ቋሚ የዜና ወኪሎች እና 21 በአጭር ጊዜ ዘገባ ፈቃድ የወሰዱ እና የዘጋቢ ፊልም ቀረፃ ፈቃድ የወሰዱ የውጭ ድርጅቶች እንደሚገኙበት ከባለሥልጣኑ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።