የአርማወር ሐንሰን የምርምር ኢንስቲትዩት "ምርምር እና ሚዲያ ለላቀ ጤና" በሚል መሪ ቃል አራተኛውን ዓመታዊ የሚዲያ ፎረም እና የጉብኝት መርሐ-ግብር በአለርት ሆስፒታል አካሄደ።
መርሐ-ግብሩ ተቋሙ የሚያከናውናቸው ውስብስብ የሳይንስ፣ የሕክምናና የፋርማሲዩቲካል ምርምሮች “በቀላል ቋንቋ” ለሕብረተሰቡ ተደራሽ እንዲሆኑና የሚዲያ ባለሙያዎች ስለ ሥራው ጥልቅ ግንዛቤ እንዲጨብጡ ለማስቻል የተዘጋጀ ነው።

ኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ፕሮፌሰር አፈወርቅ ካሱ እና ምክትል ዳይሬክተር ፕሮፌሰር ዓለምሰገድ አብዲሳ እንደገለጹት፤ ሕክምና ኢትዮጵያ ከምትታወቅባቸው የቀደሙ ሥልጣኔዎች አንዱ ቢሆንም ዘመናዊ መንገድ ባለመከተሉ ወደፊት መጓዝ ሳይችል ቆይቷል፤ አሁን ግን መንግሥት በሰጠው ልዩ ትኩረት ሀገር በቀል ዕውቀትን በዘመናዊ አግባብ መምራት ተችሏል።
ኢንስቲትዩቱ የመድኃኒት፣ የክትባትና የፋርማሲዩቲካል ኢንዱስትሪውን በስፋት እየደገፈ ይገኛል።
ባለፈው መጋቢት ወር በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የተመረቀው ዘመናዊው ባለ 8 ወለል የላብራቶሪ ሕንጻ ለሀገርና ለመላው አፍሪካ ትልቅ አቅም የፈጠረ ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅት የሬቢስ ክትባትና የዕባብ መርዝ ማከሚያ በአገር ውስጥ ለማምረት ሰፊ እንቅስቃሴ እየተደረገ ነው።
በተጨማሪም ኢትዮጵያ በክትባት ራሷን እንድትችል የሚያስችለው የ"ሺልድ ቫክሲን" ማኑፋክቸሪንግ ፕሮጀክት ግንባታ በጥሩ ሁኔታ ላይ የሚገኝ ሲሆን፣ መድኃኒቶችን በጥራት ለመፈተሽ የሚያስችለው የባዮኢክዊቫለንስ ማዕከልም የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት አገልግሎቱን ለመጠቀም ፍላጎት ያሳዩበት ትልቅ አቅም ሆኗል።

የምርምር ውጤቶችን ለሕዝብ ለማድረስ የሚዲያ ሚና የማይተካ መሆኑን የጠቀሱት ዋና ዳይሬክተሩ፤ ባለሙያዎች ቁጭትን ወደ አቅም በመቀየር፣ ዕድልን ወደ ድል በመለወጥና ሳይንሳዊ ጥያቄዎችን በመጠየቅ ሕብረተሰቡን እንዲያነቁ ጥሪ አቅርበዋል።
በፎረሙ የተሳተፉት የሚዲያና የኮሙኒኬሽን ባለሙያዎች በበኩላቸው፤ የተቋሙን የሪፎርምና የፋርማሲዩቲካል ምርምር ሥራዎች በዘገባዎቻቸው ውስጥ በስፋት በማካተት ለሕብረተሰቡ ተደራሽ ለማድረግ በትኩረት እንደሚሠሩ አረጋግጠዋል።