የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ በሀገራችን የፋይናንስ ሥነ-ምህዳር ውስጥ የሥርዓተ ጾታ እኩልነትን፣ የሴቶች ተጠቃሚነትና የውሳኔ ሰጪነት ሚና ለማሳደግ ያለመውን ሁለተኛውን የሴቶች የፋይናንስ አካታችነት መመዘኛ በዛሬው ዕለት ይፋ አድርጓል።
ከመርሐ ግብሩ ጎን ለጎን፣ በ“ኒውፊን” ኢኒሼቲቭ አማካኝነት የሰለጠኑ 1 ሺህ ወጣት ሴት የፋይናንስ ባለሙያዎችንና የወደፊት አመራሮችን አስመርቋል።
የብሔራዊ ባንክ ገዥ ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት፣ የሴቶችን አቅም ማጠናከርና በዘርፉ ላይ መዋዕለ ንዋይ ማፍሰስ የባንኩ ዋና ትኩረት መሆኑን ገልጸዋል፡፡
በአዲሱ የስኮር ካርድ የባንኮች አማካኝ አፈፃፀም እየጨመረ መምጣቱን የተገለጸ ሲሆን፣ በተለይም አዳዲስ ብድሮችን በማመቻቸት እና ለሴቶች የፈጠራ ሥራዎች ምቹ ሁኔታዎችን በመፍጠር ረገድ ውጤታማ የፋይናንስ ፈጠራዎች መመዝገባቸውን ተመላክቷል።
በሌላ በኩል አሁንም ለሴቶች የሚሰጠው የብድር መጠን አነስተኛ መሆኑ እና በከፍተኛ አመራርነት ደረጃ ያላቸው ተሳትፎ አናሳ መሆኑ በቀጣይ መሻሻል ያለባቸው ወሳኝ ክፍተቶች መሆናቸው ተለይተዋል።
ብሔራዊ ባንክ እነዚህን ተግዳሮቶች ለመቅረፍ የዲጂታል የፋይናንስ አካታችነትን ማሳደግ እና ተመጣጣኝ ዋጋ ያላቸው አቅርቦቶችን ማስፋት ላይ ትኩረት አድርጎ እንደሚሰራ አስታውቋል።
ዛሬ የተመረቁ ወጣት ሴቶች በዘርፉ የሚታየውን የአመራርነት ክፍተት ለመሙላት ትልቅ አቅም የሚሆኑ ሲሆን፣ ብሔራዊ ባንክ በቀጣዮቹ 3 ዓመታት ውስጥ የሰልጣኞችን ቁጥር ከ100 ሺህ በላይ ለማድረስ እና 70 በመቶ ያህሉን ሴቶች ለማድረግ አቅዶ እየተንቀሳቀሰ መሆኑ ተገልጿል።
በሂሩት እምቢአለ
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: