መላው ኢትዮጵያዊያን ከግጭት እና ከጥፋት ትርክት በመውጣት ሰላምን፣ ልማትን እና አንድነትን አጥብቀው እየሻቱ ይገኛሉ።
በተለይም የትግራይ ወጣቶች እና የክልሉ ሕዝብ፣ የጥፋት ፖለቲካን ባነገበው የህወሓት ቡድን የጦርነት አባዜ ዳግም ላለመጠለፍ ያላቸውን ጽኑ አቋም እና 'በቃኝ' ባይነት በተግባር እያሳዩ ነው።
የከሰረው የህወሓት ቡድን የቀረቡ የሰላም መንገዶችን ሁሉ ወደ ጎን በመተው ዳግም ወደ ጦርነት ለማምራት ወታደራዊ እንቅስቃሴዎችን እያደረገ ይገኛል።
ይህ ፀረ-ሕዝብ እና የጥፋት ስብስብ የሥልጣን ጥሙን ለማርካት እና ጥቅሙን ለማስጠበቅ ሲል ብቻ፣ የሕዝቡን የሰላም እስትንፋስ በማፈን ዛሬም ዕድሜያቸው ያልደረሰ የትግራይን አዳጊዎች እና ወጣቶች ለጦርነት እያፈሰ እና በግዴታ ወደ ሞት ለመገፍተር እየሞከረ ነው።
ሆኖም ግን የትግራይ ወጣቶች የዚህን የሕዝብ ጠላት ቡድን ጦርነት ቆስቋሽነት እና አምባገነናዊ አካሄድ አጥብቀው በመቃወም ላይ ናቸው።
ወጣቱ ላለፉት ዓመታት በጦርነት የደረሰበት ሰቆቃ እና ሥነ-ልቦናዊ ጫና ስለበቃው የከሰረውን ቡድን የግዴታ አፈሳ በማውገዝ ሰላምን እና ልማትን በመሻት ከቀሪው ኢትዮጵያዊ ወንድሞቹ ጋር ያለውን ሀገራዊ ትሥሥር ለማጠናከር በፅናት እየታገለ ይገኛል።
የውስጥ ባንዳዎችን እና የውጭ ታሪካዊ ጠላቶችን አጀንዳ በማንገብ የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ዕድገት ወደኋላ ለማስቀረት እና ሀገራችንን በትርምስ አዙሪት ውስጥ እንድትዋዥቅ ሌት ተቀን የሚደክሙ ኃይሎች የሸረቡት ሴራ በተግባር እየመከነ ነው።
ጠላቶች ኢትዮጵያን በጦርነት ትንኮሳ፣ በትርምስ እና በኢኮኖሚ ጫናዎች በማዳከም ለአጥፊ ፍላጎቶቻቸው እንድትንበረከክ የቱንም ያህል ቢጥሩም፣ ሀገራችን ግን ለትውልድ ለሚያልፉ ታላላቅ የልማት ሥራዎቿ ቅድሚያ በመስጠት ወደ ላቀ ከፍታ የምታደርገውን ጉዞ እያስቀጠለች ትገኛለች።
ታሪክ በተደጋጋሚ እንደመሰከረው የኢትዮጵያ ሕልውና እና ዕድገት በየትኛውም የጥፋት ኃይል እና ጦርነት ናፋቂ ሴራ የሚገታ አይደለም።
ሀገራችን የውስጥ አንድነቷን በማጠናከር፣ የፀጥታ እና ደኅንነት ተቋማቷን በዘመናዊ አቅም በመገንባት ዳር ድንበሯን እና ሉዓላዊነቷን በአስተማማኝ ሁኔታ እየጠበቀች ትገኛለች።
የትግራይን ሕዝብ እና ወጣቶች ከዚህ የከሰረ እና የሕዝብ ጠላት ከሆነ ቡድን የጦርነት አፈሳ እና ሰቆቃ በማውጣት መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ በተባበረ ክንድ የነገዋን ጠንካራ ኢትዮጵያን የመገንባት ታሪካዊ ራዕዩን በፅኑ መሠረት ላይ እውን ማድረጉን ይቀጥላል።
በሃና ምንዳሁን
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: