የመካከለኛው ምሥራቅ የፖለቲካ ውጥረቶች እና በሆርሙዝ እንዲሁም በባብ ኤል-መንደብ የባሕር ወሰኖች ላይ የተፈጠሩት ስጋቶች ዓለም አቀፉን የንግድ እና የሎጂስቲክስ መስመር ፈተና ውስጥ ጥለውታል።
ይህንን ተከትሎ የነዳጅ እና የመድን ዋስትና ወጪዎች በእጅጉ በመጨመራቸው፣ ሀገራት አማራጭ የንግድ መስመሮችን ለማሰስ ተገድደዋል።
የዚህን አጋጣሚ ዕድል በማድረግ ደግሞ ቻይና የዓለምን የንግድ የበላይነት የሚያጎናጽፋትን ከ5 ሺህ 400 ኪሎ ሜትር በላይ ርዝመት ያለውን እና "የአርክቲክ የበረዶ ሐር መንገድ" (Ice Silk Road) በመባል የሚታወቀውን የሰሜናዊ የባሕር መስመር በስፋት መጠቀም ጀምራለች።
የቻይናው 'ሲ ሌጀንድ ላይን' የተሰኘው የመርከብ ኩባንያ በቅርቡ የመጀመሪያውን መደበኛ የንግድ መርከብ ከቻይና የኢንዱስትሪ ማዕከል ከኒንግቦ ተነሥቶ የሩሲያን ሰሜናዊ የባሕር ዳርቻ አቋርጦ ወደ እንግሊዟ ፌሊክስስቶው ወደብ በ20 ቀናት ውስጥ ብቻ እንዲደርስ አድርጓል።
ይህም በስዊዝ ካናል በኩል ይወሰድ የነበረውን ከ40 ቀን በላይ የሚፈጅ ረጅም ጊዜ በግማሽ የሚቀንስ በመሆኑ ከፍተኛ የጊዜ እና የወጪ ብክነትን የሚያስቀር ሆኗል።
ይህ አዲስ የንግድ መስመር እውን ሊሆን የቻለው በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት በአርክቲክ አካባቢ የነበረው የበረዶ ግግር መቅለጥ በመጨመሩ የመርከቦች ዝውውር ምቹ በመሆኑ ነው።
ምንም እንኳን መስመሩ በሩሲያ ቁጥጥር ሥር ያለ እና በዓመቱ ሙሉ በሙሉ ለመጠቀም ገና ተጨማሪ ምልከታዎችን የሚፈልግ ቢሆንም፣ ቻይና በሲንጋፖር ምሥራቅ የባሕር ወሰን ላይ የነበራትን የንግድ ጥገኝነት በመቀነስ ረገድ ትልቅ የጂኦ-ፖለቲካዊ እና የኢኮኖሚ ከለላ ሆኖላታል።
የኩባንያው ሥራ አስፈጻሚዎች በሒደት የመርከቦችን ጉዞ በማስፋፋት አዲሱን የበረዶ መንገድ ዓመቱን ሙሉ ለንግድ እንቅስቃሴ ክፍት ለማድረግ አልመው እየሠሩ ይገኛሉ።
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: