ኢትዮጵያ በግብርናው ዘርፍ ለዘመናት የነበራትን እምቅ ሀብት ወደ ተጨባጭ የምግብ ዋስትና ለመቀየር የነበሩባትን ተግዳሮቶች በጽናት በመስበር ላይ ትገኛለች።
በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሐሳብ አመንጪነት ጥቅምት 23 ቀን 2015 ዓ.ም ይፋ የተደረገው "የሌማት ትሩፋት" መርሐ ግብር ሀገራችንን ከምግብ ሸማችነት ወደ አምራችነት በማሸጋገር የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የተነደፈ ዐብይ ሀገራዊ ንቅናቄ ነው።
ተግባራዊ የተደረጉ የፖሊሲ ማሻሻያዎች የግል ባለሀብቶች በፋይናንስና በቴክኖሎጂ እንዲሳተፉ በር የከፈቱ ሲሆን፣ ዘመናዊ የእንስሳት ማዳቀል፣ የሜካናይዜሽን አሰራሮች፣ የሀገር ውስጥ ማዳበሪያ ፋብሪካ ግንባታ እና የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብር ተቀናጅተው መተግበራቸው ለምርታማነት ማደግና ለውጭ ምንዛሪ ግኝት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክተዋል።
በዚህም ከ2014 እስከ 2018 ዓ.ም ባሉት አራት ዓመታት ውስጥ የወተት ማምረት አቅም ከ7.1 ቢሊዮን ወደ 15.7 ቢሊዮን ሊትር፣ የእንቁላል ምርት ከ3.2 ቢሊዮን ወደ 11.7 ቢሊዮን፣ የዶሮ ሥጋ ከ90 ሺህ ወደ 253 ሺህ ቶን እንዲሁም የማር ምርት ወደ 428 ሺህ ቶን ያደገ ሲሆን የዓሣ ጫጩት ስርጭት ደግሞ ከ300 ሺህ ወደ 16.5 ሚሊዮን አድጓል።
በተለይም በ2018 በጀት ዓመት 24.2 ሺህ ቶን የእንስሳት ተዋጽኦ ለውጭ ገበያ በማቅረብ 128.4 ሚሊዮን ዶላር ማግኘት የተቻለ ሲሆን፣ ይህ ስኬት የከተማ ግብርናን በማጠናከር የዜጎችን ገቢ ከመገንባቱ ባሻገር ለእናቶችና ሕፃናት የተመጣጠነ ምግብ በማቅረብ የመቀንጨር ችግርን ለመከላከል አስችሏል።
ይህንን ታሪካዊ ስኬት ዘላቂ ለማድረግ የመኖ አቅርቦትን ማዘመን፣ የሕክምና አገልግሎትን ማስፋፋትና የአምራችና ሸማቹን ቀጥታ ግንኙነት ማጠናከር የሚያስፈልግ ሲሆን፣ የሌማት ትሩፋት የኢትዮጵያን የምግብ ሉዓላዊነት የሚያረጋግጥ ስኬታማ ሀገራዊ መንገድ መሆኑን አረጋግጧል።
በሰለሞን ገዳ
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: